ይህ የአማራ ትሥሥርር በቻይና ይፋዊ ድረ-ገጽ ነው። በዚህ ድረ-ገጽ የአማራን ሕዝብ ታሪክ፣ ሃይማኖት፣ ባሕል፣ ልማድ፣ አርበኝነት፣ ቅርስ እና ሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮችንም ጭምር ለአባላት በሚገባ እናሳውቃለን። የድረ-ገጹ ዋና አላማ የአማራን ታሪክ በሚገባ ለሁሉም በማስተማር ታሪካችንን ወደቀደመ ልዕልናው መመለስ ነው። አንድ አማራ ለሁሉም አማራ፤ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ፤ አንዲት ነጻ ሃገር ኢትዮጵያ -->

የሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ የልደት መታሰቢያ ዕለት

 የሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ 90ኛ ዓመት የልደት መታሰቢያ 

ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ

ዝነኛው ሰዓሊና ቀራፂ እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ በሸዋጠቅላይ ግዛት  በምትገኘው አንኮበር ላይ ጥቅምት 13 ቀን 1925 ዓ/ም(ከዛሬ 90 ዓመታት በፊት) ከአባታቸው አቶ ተክሌ ማሞ እና ከእናታቸው ከወይዘሮ ፈለቀች የማታወርቅ ተወለዱ። የጠላት የግፍ ወረራ እና እልቂት ያስከተለውን የሰው፣ የንብረት እና የባህል ጥፋት እና ጉዳት ገና በሕጻንነት  ዕድሜያቸው የተመለከቱት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ከነጻነት በኋላ ሃገራቸውን እንደገና እንዴት መገንባት እንደሚቻል ሲያወጡ እና ሲያወርዱ ከቆዩ በኋላ ዋናው እና ቀዳሚው ጉዳይ እውቀት መሸመት መሆኑን የተረዱት ገና በልጅነት እድሜያቸው ነበር። ግንዛቤያቸውን በማሳደግም በማዕድን ምሕንድስና ዘርፍ ላይ እውቀት በመጨበጥ  መጥቀም እንዳለባቸው ቢወስኑም ወላጆቻቸውና ዘመድ አዝማዶቻቸው ግን የኪነ ጥበብ ስጦታቸውን በቤታቸውና በከተማው ዙሪያ በሚስሏቸው ስዕሎች በመመልከታቸው በዚሁ ሙያ እንዲሰማሩ ይጎተጉቷቸው ነበር። በታሪካዊቷ አንኮበር ከተማ የተወለዱት እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ገና በአሥራ አምስት ዓመታቸው በ1940 ዓ.ም ለከፍተኛ ትምህርት ወደ እንግሊዝ አገር ሄደው በለንደን በሚገኙ የስዕል ት/ቤቶች የስዕልና ስነ ጥበብ ትምህርቶችን ተምረዋል። ለትምህርት የተመረጡት ተማሪዎች ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን ሲሰናበቱ የተሰጣቸውን ምክር ሁሌም እንደሚያስታውሱት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ሲናገሩ ንጉሠ ነገሥቱ ተግታችሁ አጥኑና ተማሩ ፣ ጠንክራችሁ ለመስራትና ሀገራችሁ ኢትዮጵያን የምትገነቡበትን ዕውቀት ይዛችሁ ተመለሱ። ከእናንተ የሚፈለገው አዕምሯችሁን ዝግጁ አድርጋችሁ ኢትዮጵያን ለመገንባት የሚያስችል እውቀትንና ጥበብን ሸምታችሁ እንድትመለሱ ነው እንጂ አውሮፓ ውስጥ ስላሉት ረዣዥም ፎቅ ቤቶች ወይም ስለመንገዶቻቸው ስፋት በአድናቆት እንድትነግሩን አይደለም  ብለዋቸው እንደነበር ሁሌም ያስታውሱ ነበር። እሳቸውም በዝነኛው የለንደን ዩኒቨርሲቲ  የስሌድ የስነ-ጥበብ ትምህርት ቤት(Faculty of Fine Arts of the University of London) ተቀባይነት ያገኘ የመጀመሪያው አፍሪካዊ መሆን ችለዋል። በዚህ ትምህርት ቤት ቆይታቸውም በቀለም ቅብ፣ በቅርጻ ቅርጽ እና በኪነ ህንጻ ጥናቶች ላይ በመስራት ተመርቀዋል። እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ትምህርታቸውን አጠናቀው ወደ ኢትዮጵያ እንደተመለሱ በተለያዩ ግዛቶች በመዘዋወር በአንዳንድ ቦታም እስከ ሦስት ወራት በመቀመጥ የኢትዮጵያን ታሪክ እና የብሔረሰቦቿን ባህልና ወግ ሲያጠኑ ቆይተዋል። 

ዓለም አቀፍ እውቅና ያለው ኢትዮጵያዊ ሰዓሊ ለመሆን ህልም የነበራቸው አፈወርቅ ይህን ህልማቸውን እውን ለማድረግ የመረጡት መንገድ የምዕራባውያን ጠበብትን የአሳሳል ዘይቤ መቅዳት ሳይሆን የራሳቸውን ዘይቤ መፍጠር ነበር። አፈወርቅ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ በክብር ተገኝተው የከፈቷቸውን የኪነ-ጥበብ አውደ-ርዕዮችን ማሳየት የቻሉ ታላቅ ሰዓሊና ቀራፂ ነበሩ። በ1946 ዓ/ም በሀያ ሁለት ዓመታቸው የተለያዩ የስነ ጥበብ ሥራቸውን የሚያሳይ የመጀመሪያውን ኤግዚቢሽን በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት አቅርበዋል። ከትርዒቱ ባገኙት ገቢ በድጋሚ ወደ አውሮፓ በመሄድ ለሁለት ዓመት በጣሊያን፣ በፈረንሳይ፣ በስፔን፣ በፖርቱጋል፣ በእንግሊዝና ግሪክ ጥልቅ የኪነ ጥበብ ጥናት አከናውነዋል። በጦርነትና በሌሎች ምክኒያቶች ተዘርፈው በነዚህ ሃገራት የሚገኙትን የኢትዮጵያ ጥንታዊ የሃይማኖትና የታሪክ የብራና መጻሕፍትን በጥልቅ አጥንተውና የመስታወት ላይ ስዕል ( የሞዛይክ አሠራር ጥበብን ) ቀስመው ወደ አገራቸው ተመልሰዋል።

 ጎልተው ከሚታወቁት ሥራዎቻቸው መካከል የሚከተሉት ተጠቃሽ ናቸው።  

➥ ኪዳነ ምሕረት፣

➥ የመናገሻ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ-ክርስቲያን የግድግዳ፣

➥ የመስኮትና የጣሪያ ስዕሎችና ሞዛይኮች፣

➥ እናት ኢትዮጵያ፣ 

➥ የመስቀል አበባ፣

➥  የዳግም ምፅዓት ፍርድ፣

➥ ደመራ፣ 

➥  በሐረር ከተማ የሚገኘውን የልዑል ራስ መኮንን ሀውልት፣

➥ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ምስል፣

➥  የሐረር ጦር አካዳሚ ሥዕሎች፣

➥  የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) የአፍሪካ አዳራሽ ስዕሎች፣

➥  የቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴን የዘውድ ስርዓት እንዲሁም

➥  ንጉሥ ሰለሞን በኢየሩሳሌም ለንግሥተ ሳባ ያደረገላትን አቀባበል 

አፈወርቅ ተክሌ ከፍ ያለ ችሎታና ስነ ምግባር ያላቸው አርቲስት ከመሆናቸውም ባሻገር በብዙ የሥዕል ሥራዎቻቸው ክፍለ ዓለማቸውን አጉልተው ስለገለፁና በኢትዮጵያ ስነ ጥበብን በዘመናዊ ቴክኒክ መሥራት ከጀመሩት ከቀዳሚዎቹ መካከል አንዱ ስለሆኑ በ1957 የመጀመሪያውን የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ብሔራዊ የሥነ ጥበብ ሽልማት አሸንፈዋል። አፈወርቅ በበርካታ የዓለም ሀገራት ተዘዋውረው ብዙ የስነ ጥበብ ትዕይንቶችን አቅርበዋል።  ከመቶ የማያንሱ ዓለም አቀፍ ሽልማቶችን እንዳገኙ የሚነገርላቸው አፈወርቅ ተክሌ የአራት ዓለም አቀፍ የሥነጥበብ አካዳሚዎች አባል ነበሩ። ለመጀመሪያ ጊዜ የአገራቸው ስምና አጭር የሕይወት ታሪካቸው ተጽፎ ወደ ጨረቃ ከተላከላቸው 200 ታላላቅ የአገር መሪዎች፣ የታሪክ ተመራማሪዎች፣ ሳይንቲስቶች፣ ደራስያን፣ ሠዓሊያን  መካከል አንዱ አፈወርቅ ተክሌ ናቸው።

አፈወርቅ መኖሪያ ቤታቸውን እንዲሁም ስቱዲዮና ጋለሪ ያካተተውንና ቪላ አልፋ የተሰኘውን ሕንፃ ራሳቸው ዲዛይን ያደረጉት ሲሆን ስራውም 15 ዓመታት እንደፈጀ ይነገራል። 22 ክፍሎች ያሉት ቪላ አልፋ ጥንታዊቷን አክሱምን፣ የጎንደር ቤተ መንግስትንና የሐረር ግንብን በሚያንፀባርቅ መልኩ የታነፀ ነው።

እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ባደረባቸው ጽኑ ሕመም በሕክምና እየተረዱ ሳለ ማክሰኞ ዕለት  ሚያዝያ 2 ቀን 2004 ዓ.ም በተወለዱ በ79 ዓመታቸው በአዲስ አበባ ካዲስኮ ሆስፒታል አርፈዋል። የቀብር ስርዓታቸውም በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል። 

ምንጭ፦ ልዑል ዓምደጽዮን ሠርፀድንግል

አዘጋጅ፦ የታሪክ ክፍል


የአማራ ትስስር በቻይና

ጥቅምት 13  2015 ዓ.ም 

ቻይና

የአማራ ትስስር በቻይና(ANiC)

የአማራ ሕዝብ የሚያኮራ ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ስነጽሑፍ፣ ሃይማኖትና ባህል ያለው፤ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ቅርሶች ባለቤት የሆነ፤ ሃገር የሰራ፣ ነጻነቱን ያስጠበቀ፤ የራሱ የሆነ ፊደል ያለው፤ የጥንታዊ ትምህርት ስርዓት ባለቤት የሆነ ጀግናና ኩሩ ሕዝብ ነው። የአማራ ሕዝብ በሃገረ መንግስት ምስረታ ሃገርን ከወራሪ መጠበቅና ዳር ድንበሯን በማስጠበቅ ታላቅ ገድል በመስራት እኛ ልጆቹ ቀና ብለን እንድንሄድ አድርጎናል።

2 Comments

ቀዳሚ ገጽ ተከታይ ገጽ
hi