ይህ የአማራ ትሥሥርር በቻይና ይፋዊ ድረ-ገጽ ነው። በዚህ ድረ-ገጽ የአማራን ሕዝብ ታሪክ፣ ሃይማኖት፣ ባሕል፣ ልማድ፣ አርበኝነት፣ ቅርስ እና ሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮችንም ጭምር ለአባላት በሚገባ እናሳውቃለን። የድረ-ገጹ ዋና አላማ የአማራን ታሪክ በሚገባ ለሁሉም በማስተማር ታሪካችንን ወደቀደመ ልዕልናው መመለስ ነው። አንድ አማራ ለሁሉም አማራ፤ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ፤ አንዲት ነጻ ሃገር ኢትዮጵያ -->

ጥንታዊቷ የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርሲቲያን

ጥንታዊቷ የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርሲቲያን

የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በደቡብ ወሎ ዞን ወረኢሉ ወረዳ የምትገኝ ናት። ከአዲስ አባባ 476 ኪ.ሜ. እንዲሁም ከደሴ ከተማ 76 ኪ.ሜ. ወረኢሉ ለመድረስ 15 ኪ.ሜ. ሲቀረው ሰኞ ገበያ ተብላ ከምትጠራ አንዲት ትንሽ ከተማ በስተምዕራብ በኩል 4 ኪ.ሜ. ርቀት ላይ ትገኛለች። በጂ.ፒ.ኤስ. መለኪያም በ10°44’57” የኬክሮስ መስመርና በ39°24’97” ምሥራቅ የኬንትሮስ መስመር ላይ ዐርፋለች።

የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ከታሪክ ጸሐፊዎች እይታ አኳያ

የታሪክ መዛግብቱም ሆኑ አፈታሪኮች እንደሚስማሙበት ከሆነ የጥንታዊቷ የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያ የተመሠረተችው በ1513 ዓ.ም ነበር። የቤተ ክርስቲያኗ የሕንፃ መሠረት የተጣለው በዓፄ ናዖድ ዘመነ መንግሥት (1489-1500 ዓ.ም) ሲሆን አስገንብተው ያስጨረሱት ልጃቸው ዐፄ ልብነ ድንግል (1500-1533) ናቸው። በቤተ ክርስቲያኗ የምርቃ በዓል ላይ በ1513 ዓ.ም በሥፍራው በመገኘት ስለ ቤተ ክርስቲያኗ ያየውንና የሰማውን በመጻፍ ለትውልድ እንዲተላለፍ በማድረግ ግንባር ቀደሙ ፖርቱጋላዊው ፍራንሲስኮ አልቫሬዝ ነው። አልቫሬዝ ስለ ጥንታዊው ቤተ ክርስቲያን ሥነ ሕንፃዊ ጥበብ ያሰፈረው ሐተታ ከታሪካዊ መረጃነቱ በተጨማሪ ለአርኪዎሎጂና አርክቴክቸር ጥናትና ምርምር ጥሩ መነሻ ሊሆን የሚችል ነው። አልቫሬዝ ስለ ቤተ ክርስቲያኗ ሥነ ሕንፃዊ አወቃቀር እንዲህ ሲል ጽፏል፡-
ግድግዳዎቹ በጥርብ ድንጋይ ተሠርተው በሐረግ አጊጠዋል፤ የዋናው በር መዝጊያ በወርቅና በብር ተለብዷል፤ በወርቁ ልባድ ውስጥ አንዳንድ የከበሩ ድንጋዮች አሉ። ጣሪያዎቹ በስድስት ምሰሶዎች ላይ ዐርፈዋል። የውጭ ታዛውን 13 ረጃጅም ምሰሶዎች ደግፈውታል። በሠገነቱ ዙሪያ እያንዳንዳቸው ከ16 ቅጽ ወርቀ ዘቦ ጨርቅ የተሠሩ 16 ተከፋች መጋረጃዎች አሉት።
በአሕመድ ኢብን ኢብራሒም አልጋዚ(ግራኝ አሕመድ) የሚመራው የሙስሊሞች ሠራዊት የዐፄ ልብነ ድንግልን ጦር ድል አድርጎ የያኔዋን ዋስል የዛሬዋን ወረኢሉ በመቆጣጠር የመካነ ሥላሴን ቤተ ክርስቲያን ከማጥፋት ቀደም ብሎ (ከ1524 ዓ.ም በፊት) የቤተ ክርስቲያኒቱን ገጽታ በብዕሩ የከተበው የግራኝ አሕመድ ታሪክ ጸሐፊ ዓረብ ፋቂህ እንዲህ ሲል ገልጽዋታል። በዚህ በቤተ አምሐራ በሐበሻ ምሳሌ የሌላት አንዲት ቤተ ክርስቲያን አለች። እርሷን የሠራት የወናግ ሰገድ (ልብነ ድንግል) አባት ንጉሥ ናዖድ ነው። የእርሷ ሥራና ጌጥ 13 ዓመት ፈጀበትና ሳይጨርሳት ስለ ሞተ ልጁ ወናግ ሰገድ ከአባቱ አስበልጦ 25 ዓመት ሙሉ አሠርቶ አስጨረሳት። ሁለመናዋ በወርቅ የተለበደ ስለሆነ እንደ እሳት ታንጸባርቃለች፤ በውስጧ ያለው ጻሕል፣ ሰንና ብርት የወርቅና የብር ነው። ስፋቷ መቶ ክንድ ቁመቷ ግን ከመቶ ሃምሳ ክንድ ይበልጣል። ሁለመናዋ በጌጠኛ ዕንጨትና ድንጋይ በወርቅና በከበረ ድንጋይ የተለበደ ነው። ስሟ በክርስቲያኖች ቋንቋ መካነ ሥላሴ ትባላለች። በዚህች ቤተ ክርስቲያን የዘርዐ ያዕቆብ የልጅ ልጅ የአድማስ ሰገድ (በእደ ማርያም) ልጅ የናዖድ መቃብር አለ።

ያቺ በሥነ ሕንፃዊ ጥበቧና በተሠራችበት የከበሩ ድንጋዮች ወደር ያልተገኘላት የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በኅዳር ሰባት ቀን 1524 ዓ.ም በግራኝ አሕመድ ፊት አውራሪነት እንድትዘረፍና እንድትቃጠል እንደ ተደረገች ዓረብ ፋቂህ ጽፏል። ግራኝ አሕመድ ቤተ ክርስቲያኗ እንድትዘረፍና እንድትቃጠል ከማዘዙ በፊት የቤተ ክርስቲያኒቱን ሥነ-ሕንፃ ማድነቁን ዓረብ ፋቂህ አልሸሸገም። ይህንን የመሠለ የወርቅ ሐውልት ያለበት በወርቅ የተሠራ ቤተ ክርስቲያን በሕንድ በሮም (በቤዛንታይን) ግዛት ዐይታችሁ ታውቃላችሁ? ብሎ በዙሪያው ያሉትን ዓረቦች መጠየቁን የሚያትተው ዓረብ ፋቂህ፡- ይህንን የመሰለ በሮምም በሕንድም ዐይተንም አለ ሲባልም ሰምተን አናውቅም፤ በዓለምም የለም ብለው መለሱለት ሲል ጽፏል። ሆኖም አልቫሬዝ የመካነ ሥላሴ ሕንፃ የማእዘን ድንጋዮች ትናንሽና በደረቅ ካብ የተሠሩ በመኾኑ የጣሪያው መዋቀሪያ እንጨት በግድግዳው እንደማያልፍ ገልጦ፣ ከቤተ ክርስቲያኗ የሚበልጡ ሕንፃዎችን በአውሮፓ ማየቱን ቢያትትም የመካነ ሥላሴ ሕንፃ ጥበብ ግዙፍነትና በከበረ ድንጋይ ያጌጠች እንደነበረች አረጋግጧል። ይህ የሚያመለክተው የመካነ ሥላሴ ጥንታውያት ቤተ ክርስቲያን እንደ ላሊበላ ውቅር ሕንፃዎች፣ እንደ ዐፄ ፋሲል (ጎንደር) ቤተ መንግሥታት ሁሉ በወቅቱ የነበሩትን ኢትዮጵያውያንን የሕንፃ ጥበብ የሚያሳይ አሻራ ነው። የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በላሊበላ ውቅር አቤተ ክርስቲያናት በተሠሩበት ዘመንና በጎንደር የፋሲል አብያተ መንግሥታት የተሠሩበት ዘመን መካከል መገኘቱ ያ የኢትዮጵያውያን የሥነ ሕንፃ ጥበብ ቀጣይነት እንደነበረው ጠቋሚ ሊሆን ይችላል።

ከግራኝ አሕመድ ሠራዊት ዘረፋና ቃጠሎ የተረፈው የቤተ መቅደሱ የመሠረት ግንብ የቅድስቱና የቅኔ ማኅሌቱ መለያ ግንቦች በዕድሜ ጫና ጥበቃና ክብካቤ በማጣት እየፈራረሱ ወደ አፈርነት እየተለወጡ ለዘመናት ቆይተዋል።

የመካነ ቅርሱ አሠራርና መጠን

መካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን እንደ አካባቢው አጠራር ገህ (ገሃ) ተብሎ ከሚጠራ የኖራ ድንጋይ የተሠራ ሰፊና ግዙፍ ቤተ ክርስቲያን ነው። ይህ ቤተ ክርስቲያን አራት ጎኖች እኩል የሆኑ ቤተ መቅደስና ቅድስት የነበረው ሲሆን ቅኔ ማኅሌቱ ክብ ነው። የቤተ መቅደሱ ወለል 20 ሜትር በ20 ሜትር ሆኖ የቤተ መቅደሱ መሠረት ግንብ አራቱም ጎኖች ተለክተው 26 ሜትር በ26 ሜትር ሆኖ ተገኝቷል። ከቤተ መቅደሱ እስከ ቅድስቱ መሠረት ድረስ ያለው ርዝመት አምስት ሜትር ሲሆን ከቅድስቱ እስከ ቅኔ ማኅሌቱ ያለው ርቀት 16 ሜትር ነው። በዚህ መሠረት ቤተ ክርስቲያኑ ከደቡብ እስከ ሰሜን 47 ሜትር ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ 47 ሜትር ያህል መሆኑ ተለክቶ ተረጋግጧል። ከቤተ መቅደሱ ወለል እስከ መሠረቱ ያለው ጥልቀት ሁለት ሜትር ሲሆን በቤተ መቅደሱ ወለል ላይም 26 መንበሮች መኖራቸው በተካሄደው የቅርስ አድን ሥራ ማወቅ ተችሏል። መንበሮቹም አራት አራት ሆነው በአራቱም ጎኖች ተቀምጠዋል። መንበሮቹ በጠፍጣፋ ገህ ድንጋይ በመስቀል ቅርጽ የተሠሩና አራቱም የመንበሮቹ ጎኖች (አንድ ሜትር ከዐሥር ሣ.ሜ.) እኩል ናቸው።

በደቡብ፣ በሰሜን፣ በምዕራብና በምሥራቅ በኩል ወደ ቤተ መቅደሱ የሚያስገቡ አራት ደረጃዎች እንደነበሩት ታውቋል። በሰሜንና በደቡብ በኩል ያሉት ደረጃዎች አራት ሜትር ቁመትና ሦስት ሜትር ጎኖች ያሏቸው ሲሆን በምዕራብና በምሥራቅ በኩል የነበሩት ደረጃዎች ወድመዋል። በቤተ መቅደሱና በቅድስቱ ወለል እስከ መሠረቱ ግንብ ጥልቀት ባለው ሁለት ሜትር ቁመት ላይ የዘመኑን የሥነ ሕንፃ ምሕንድስና ጥበብ የሚያንጸባርቁ የተለያዩ ጌጣጌጦች ይታያሉ። እነዚህም ጌጣጌጦች የሐረግና የተለያዩ አበባዎች ቅርጾችን እንዲሁም የተለያዩ ምስሎችን ይዘው ይገኛሉ። በሌላ በኩል በጥንታዊው የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ቤተ መቅደስ ወለል ላይ በዐፄ ዮሐንስ ዘመነ መንግሥት ተሠራች ተብሎ በአካባቢው ነዋሪዎች የሚነገር አንዲት አነስተኛ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ቆማ ትገኛለች። ቤተ ክርስቲያኗ መጀመሪያ ስትሠራ በሣር የተከደነች እንደነበረችነ በኋላ ግን የሣሩ ክዳን ተነሥቶ ቆርቆሮ መልበሷን ግድግዳዋ ግን ሳይነካ ቀድሞ በነበረበት ሁኔታ ላይ እንዳለ ነዋሪዎቹ ያስረዳሉ። የቤተ ክርስቲያኗ ግድግዳ ከድንጋይ የተሠራ ሆኖ ከእነዚህ የግድግዳ ድንጋዮችም የጥንቱ የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ፍርስራሽ እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል። ይህች ቤተ ክርስቲያን እስከ አሁን ድረስ አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደምትገኝ በግልፅ ታውቋል።

ምስል፦ ጥንታዊቷ የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርሲቲያን


መካነ ቅርሱ አሁን ያለበት ሁኔታ

የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ዕድሜ ጠገብ እንደመሆኑ መጠን ዝናብና ፀሐይ እየተፈራረቁ እያበላሹት ይገኛሉ። ከፍታ በሌለው የድንጋይ ካብ የታጠረና ጠንካራ በርም ስለሌለው ልጆችና ከብቶች በቀላሉ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ግቢ በመግባት በቅርሱ ላይ ጉዳት ሊያደርሱ እንደሚችሉ መረዳት አያደግትም። በጥንታዊቷ የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ቤተ መቅደስ ወለል ላይ በዐፄ ዮሐንስ ዘመነ መንግሥት ተሠራች ተብሎ የሚነገርላት ቤተ ክርስቲያን በአሁኑ ጊዜ አገልግሎት እየሠጠች ነው። ስለሆነም ተገልጋዩ ወገን ጥንቃቄ በጎደለው ሁኔታ በየጊዜው በቤተ መቅደሱ ወለል ላይ በመውጣትና በመውረድ ሊጎዳው እንደሚችል መገንዘብ ተችሏል። ጥንታዊው የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ተሠርቶ ባለቀ በዐሥራ አንድ ዓመቱ በግራኝ አሕመድ ወረራ ጊዜ እንደተቃጠለ የታሪክ መዛግብት ያስረዳሉ። ከዚህ ሌላ የአካባቢው ነዋሪዎች በተለያዩ ጊዜያት ከቤተ ክርስቲያኑ ላይ ንጣፍ ድንጋዮችን በማንሣት ለቤት መሥሪያ፣ ለአጥርነት፣ ለመቃብር መዝጊያ አገልግሎት ያውሉት ስለነበረ አሁን ቅርሱ በጣም ተጎድቶ ይገኛል። ይኸው የመቅደሱ፣ የቅድስቱና የቅኔ ማኅሌቱ ግድግዳ ብቻ ነው። የዘመኑን ሥነ ጥበብ የሚያመለክቱ ብዙ ጌጣጌጥ የተሣሉባቸው ጠፍጣፋና ባለ አራት ማዕዘን የገህ ድንጋዮች ከነበሩበት ቦታ ተነሥተዋል፤ ተሰባብረዋልም። ከግንዛቤ ጉድለት የተነሣና የቅርስን ምንነትና ጥቅም ባለማወቅ የአንዳንድ አካባቢ ነዋሪዎች በሰሜን፣ በደቡብና በምዕራብ በኩል የቤተ መቅደሱን መሠረት በመቆፈር በመሬት ውስጥ ተቀብረው የነበሩ የአርኪዎሎጂ መረጃዎችን አበላሽተዋል። በደቡብና በምዕራብ በኩል ያሉት የቤተ መቅደሱ ጎኖች በከፊል ዘመው ይታያሉ። የቤተ መቅደሱ ወለልም በመጠኑም ቢሆን ሰርጉዶ የሚታይ ሲሆን በላዩ ላይ ያሉት መንበሮች ግን ከሌሎች በተሻለ ሁኔታ ላይ ይገኛል። ቤተ ክርስቲያኗ ታሪካዊነት ስላላት በቴክኒክ አሠራሯና ጥበቧ ትምህርት ሰጪ ናት። ይሁንና እንክብካቤና ጥበቃ የጎደለው ለመሆኑ ከቤተ ክርስቲያኗ ገጽታ ለመረዳት ችለናል።

የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስያን ቅሪት ከ485 ዓመታት በላይ ማስቆጠሩ ቅርሱን ዕድሜ ጠገብ የሚያደርገው ሲሆን የሥነ ሕንፃው ምሕንድስና እና ጥበብ በዘመኑ ከነበሩት የተለየ ነው። ጥንታዊው ቤተ ክርስቲያን ከአብዛኞቹ ጥንታዉያን አብያተ ክርስቲያናት በተለየ መልኩ ሰፊና ግዙፍ መሆኑ ራሱ ልዩ ያደርገዋል። ቤተ ክርስቲያኑ የተሠራበት ጥሬ ዕቃ (ገህ ድንጋይ) በአካባቢው በቅርብ ርቀት አለመገኘቱና በሌሎች በአካባቢው ባሉ አቤያተ ክርስቲያናት ጥቅም ላይ ውሎ አለመታየቱ ቤተ ክርስቲያኑ በጥንቃቄና ታስቦበት የተሠራ መሆኑን ይጠቁማል። ቤተ ክርስቲያኑን ለመሥራት የፈጀው ዓመትም ረዥም መሆኑ የቤተ ክርስቲያኑን ታሪክ ልዩ ያደርገዋል። ይህንን ሁሉ ዘመን ከዚያም በኋላ ያለውን ጊዜ የሚጠቁሙ አርኪዎሎጂያዊ ታሪካዊና ባህላዊ መረጃዎችን ሸሽጎ መያዙ አይቀሬ በመሆኑ እነዚህም መረጃዎች የማዳን ተግባር አስፈላጊነቱ ከፍተኛ ነው። በቅርሱና በአካባቢው የተካሄደውን የቅኝት ሥራ ውጤት መሠረት በማድረግ ሥራ በማከናወን የቤተ መቅደሱን መሠረት ዙሪያና ወለሉን በማጽዳት በወለሉ ላይ የነበሩ የመስቀል ቅርጽ የነበራቸው 26 ወንበሮች በጎለህ እንዲታዩ ሆነዋል። የሙከራ ቁፋሮ ተካሂዶ የቤተ መቅደሱ የመሠረት ግንብ ጥልቀት ምን ያህል እንደሆነ ተረጋግጧል። የቤተ መቅደሱን የቅድስቱንና የቅኔ ማኅሌቱን የግንብ መጠን በመለካት መጠነ ዙሪያቸውን ስፋታቸውንና ርዝመታቸውን ለማወቅ ተችሏል። የቅኝት ስልቱን ውጤት በመንተራስ የዘመሙና ሊወድቁ ተቃርበው የነበሩ የቤተ መቅደሱ መሠረት ድንጋዮችን በደረቅ ካብ በመካብ ደግፎ በጊዜያዊነት እንዲያቆያቸው ተደርጓል። ይህም ተግባር ቅርሱ አጠቃላይ ጥገና እስከሚካሄድበት ድረስ ጊዜያዊ ድጋፍ እንደሚሆነው ይታመናል። የቅኝቱንና የአሰሳውን ስልት መሠረት በማድረግ የተጎዳውን የቤተ ክርስቲያኗን ፍርስራሽ ክፍል ደኅና ከሚባለው ለመለየት ተችሏል። ባለ ማወቅ ተቆፍረው ለጥፋት ተዳርገው የሚገኙትን የቤተ መቅደሱን ክፍሎች አፈር በመመለስ ለዝናብ፣ ለፀሐይ፣ ለሰውና ለእንስሳት ተጋልጠው ጉዳት እንዳይደርስባቸው ለማድረግ ተችሏል። በጣም ጉዳት ደርሶበት ያለው ምሥራቃዊው የቤተ መቅደሱ ጎን አፈሩ በዝናብ ታጥቦ (ተሸርሽሮ) ተጨማሪ ጉዳት እንዳይደርስበት ድንጋይ የማልበስ ሥራ ተሠርቷል። በተጨማሪም በዚሁ በምሥራቃዊው ጎን ላይ ተከማችተው የነበሩ ለሕንፃው ባዕድ የሆኑ ድንጋዮች ከሥር ያለውን የመሠረት ድንጋይ ስለ ጎዱት ከቦታቸው በማስወገድ ከቤተ መቅደሱ እስከ ቅድስቱ መለያ ግንብ ድረስ ታጥሮ የነበረውን የድንጋይ ካብ በማንሣት ለሰዎች መተላለፊያ እንዲሆን በማስቻል ምእመናን በፍርስራሹ ላይ እንዳይረማዱ ማድረግ ተችሏል። ለአካባቢው ማኅበረሰብ ስለ ቅርሱ ምንነትና ጠቀሜታ እንዲሁም እንክብካቤና ጥበቃ ብሎም ለወደፊት ስለሚያስገኘው ኢኮኖሚ (ግንዛቤ) በማስጨበጥ ኅብረተሰቡ ጠቃሚ ትምህርት (መረጃ) እንዲያገኝ ማድረግ ተችሏል። ከላይ ከተጠቀሰው ጋር በተያያዘ መካነ ቅርሱን የሚጠብቅና የሚንከባከብ ዘጠኝ አባላትን ያቀፈና ከተለያዩ የኅብረተሰቡና የመንግሥት አካላት የተውጣጣ የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ጥበቃና ክብካቤ ኮሚቴ ማቋቋም ተችሏል።
ምስል፦ የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርሲቲያን መሰረት


ግኝቶች

በአርኪዎሎጂ አሰሳ ሥራ የቤተ ክርስቲያኗን ቅኔ ማኅሌት መጠን ዙሪያ ለማግኘት ተችሏል። በዚሁ አሰሳ የተቃጠሉ ድንጋዮች፣ ከሰል፣ የተሰባበሩ ሸክላዎች፣ ቁርጥራጭ ብረቶች፣ የጥይት ቀላህ፣ የሰው ዐፅም ተገኝቷል። በሰሜን የቤተ ክርስቲያኑ ጎን የአርኪዎሎጂ ሙከራ ቁፋሮ ተደርጎ የቤተ መቅደሱና የቅድስቱ የመሠረት ግንብ ጥልቀት ታውቋል። ከቤተ መቅደሱ ወለል እስከ መሠረቱ ተረጋግጧል። በአፈር ሥር ያለው የመሠረት ድንጋይ 50 ሤ.ሜ. ጥልቀት ያለው መሆኑም ታውቋል። በቁፋሮው የወጡት መረጃዎች፣ ሸክላዎች፣ የተቃጠሉ ድንጋዮች ከሰል፣ የሰው ወይም የእንስሳት ዐፅም ናቸው። በአጠቃላይ የመካነ ሥላሴን ቤተ ክርስቲያን ጥንታዊነት ታሪኩን፣ የሕንፃውን ምሕንድስና እና ጥበብ እንዲሁም አሁን የምትገኝበትን ሁኔታ ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት ተጠብቃ ከጥፋትና ብልሽት ድና ለተገቢው ጥናትና ምርምር እንድትበቃ ብሎም ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊው ጠቀሜታ እንድታስገኝ የሚከተሉት አሳቦች ተግባራዊ ማድረግ ተገቢ መሆኑን እንገልጻለን። በመካነ ቅርሱ አካባቢ የሚገኙ ነዋሪዎች ቅርሱን በመጠበቅ ከፍተኛ ተሳትፎ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። ይኸው ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ግቢ ውስጥ ከብቶችና ሕፃናት እንዲሁም አንዳንድ ስለ ቅርስ ግንዛቤ የሌላቸው ሰዎች ከሌላ ቦታ እየመጡ ባለማወቅ ገብተው እንዳያበላሿቸው ነዋሪዎች መጠበቅ ይኖርባቸዋል። የተቋቋመው የመካነ ሥላሴ ቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ኮሚቴ ቅርሱ ምን ያህል እየተጠበቀ እንደሚገኝ በየጊዜው ክትትልና ቁጥጥር ማድረግ ይገበዋል። የመካነ ቅርሱን ቦታ ከልሎ የማስጠበቅ ሥራ በተቻለ ፍጥነት መሠራት አለበት። በቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ግቢም ሆነ በዙሪያቸው ምንም ዓይነት ቁፋሮ መካሄድ የለበትም። ቤተ ክርስቲያኑ በቃጠሎ የተጎዳ ስለሆነና የዕድሜ ብዛትም ስላለው በቀላሉ ሊበላሽ ስለሚችል በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን አስቸኳይ ጥገና ሊደረግለት ይገባል። ፀሐይና ዝናብ ተፈራርቀው ከናካቴው እንዳያጠፉት መጠለያ ሊሠራለት የግድ ይላል። በጥንታዊው የመካነ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ቤተ መቅደስ ወለል ላይ በዐፄ ዮሐንስ ዘመነ መንግሥት ተሠራች የተባለቸው አነስተኛ ቤተ ክርስቲያን በአሁኑ ጊዜ አገልግሎት እየሠጠች ስለሆነ ከዚህ አገልግሎት ጋር በተያያዘ ልጆች ወደ ግቢው እየገቡ በቅርሱ ላይ በመጫወት ሲጎዱና አንዳንድ እንስሳትም ወደ ቤተ ክርስቲያን ግቢ ውስጥ እየገቡ ከግንቡ ጋር በመታከክ ጥፋት ሲያደርሱ ተመልተናል፡፡ ከዚያ በተጨማሪ ብዙ ምእመናን በዕለተ እሑድና በሌሎች በዓላት ቀናት በቤተ መቅደሱ ወለል ላይ እየወጡ ስለ ሚጸልዩ የሰረጎደው ወለል በክብደትና ጥንቃቄ በጎደለው አያያዝ ሊፈርስ እንደሚችል እሙን ነው። በጥንታዊው ቤተ ክርስቲያን ፍራሽ ቅርስ ላይ እየተሠጠ ያለው ሃይማኖታዊ አገልግሎት በቅርስ ላይ ተጨማሪ ጉዳት የሚያስከትል ስለሆነ መቆም አለበት። በቦታው ላይ ሊሠራ የታቀደው ግንባታም መካሄድ የለበትም። ከተቋቋመው ኮሚቴ ጋር በመተባበርና ኅበረተሰቡን በቀጥታ በማሳተፍ የቅርስ አስተዳደርና ጥበቃ ሰነድ መዘጋጀት ይኖርበታል።

ምንጭ፦ (ከመ/ር ኅሩይ ባየ፣ ቅዱሳት መካናት ከሚለው መጽሐፍ፣ ከገጽ 209-217 የተወሰደ)

የአማራ ትስስር በቻይና

ሐምሌ 30 ቀን 2014 ዓ.ም

ቻይና

የአማራ ትስስር በቻይና(ANiC)

የአማራ ሕዝብ የሚያኮራ ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ስነጽሑፍ፣ ሃይማኖትና ባህል ያለው፤ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ቅርሶች ባለቤት የሆነ፤ ሃገር የሰራ፣ ነጻነቱን ያስጠበቀ፤ የራሱ የሆነ ፊደል ያለው፤ የጥንታዊ ትምህርት ስርዓት ባለቤት የሆነ ጀግናና ኩሩ ሕዝብ ነው። የአማራ ሕዝብ በሃገረ መንግስት ምስረታ ሃገርን ከወራሪ መጠበቅና ዳር ድንበሯን በማስጠበቅ ታላቅ ገድል በመስራት እኛ ልጆቹ ቀና ብለን እንድንሄድ አድርጎናል።

Post a Comment

ቀዳሚ ገጽ ተከታይ ገጽ
hi