ይህ የአማራ ትሥሥርር በቻይና ይፋዊ ድረ-ገጽ ነው። በዚህ ድረ-ገጽ የአማራን ሕዝብ ታሪክ፣ ሃይማኖት፣ ባሕል፣ ልማድ፣ አርበኝነት፣ ቅርስ እና ሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮችንም ጭምር ለአባላት በሚገባ እናሳውቃለን። የድረ-ገጹ ዋና አላማ የአማራን ታሪክ በሚገባ ለሁሉም በማስተማር ታሪካችንን ወደቀደመ ልዕልናው መመለስ ነው። አንድ አማራ ለሁሉም አማራ፤ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ፤ አንዲት ነጻ ሃገር ኢትዮጵያ -->

ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ(Professor Asrat Woldeyes)

ዛሬ(ግንቦት 6) የፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ 23ኛ ዓመት የሰማዕትነት መታሰቢያ እለት ነው።

ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ
አስራት ወልደየስ ከአባታቸው ከአቶ ወልደየስ አልታዬ እና ከእናታቸው ከወይዘሮ በሰልፍይዋሉ ጽጌ ሰኔ 12 ቀን 1920 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ተወለዱ። የአስራት አባት አቶ ወልደየስ አልታዬ በጸሓፊ ትዕዛዝ ኃይሌ ወልደ-ስላሴ አስተዳደር ውስጥ በጸሐፊነትና በአስተዳደር ተግባር የተሰማሩ ነበሩ። እናታቸውም በአነስተኛ ንግድ የተሰማሩ ነበሩ። ፕሮፌሰር አሥራት የሶስት ዓመት ህጻን እያሉ ወላጆቻቸው በፍች ምክንያት ስለተለያዩ ከእናታቸው ጋር ወደ ድሬዳዋ አቀኑ። ጣልያን በ1928 ዓ.ም ኢትዮጵያን ሲወር ገና የ የ8 ዓመት ልጅ ነበሩ። ጣልያን አያታቸው ቀኝ አዝማች ፅጌ ወረደ ወርቅን ወደ ጣልያን በምርኮ ወሰደባቸው የ1929ኙን የግራዝያኒ ግድያ ሙከራ ተከትሎ ከተጨፈጨፉት ከ30000 በላይ ኢትዮጵያውያን አባታቸው አቶ ወልደየስ አልታየ አንዱ ሆኑ። ይህንን ተከትሎም በባለቤታቸው ኅዘን ከፍተኛ ህመም ላይ የወደቁት እናታቸው ወድያውኑ ሞቱባቸው። ወላጆቹን በሞት የተነጠቀው ታዳጊ ከአያቱ ከወይዘሮ ባንቺወሰን ይፍሩ-ለሱሲሉ ጋር መኖር ጀመረ። አጎቱ አቶ ዘውዴ ወረደወርቅ እዚያው ድሬዳዋ ይኖሩ ነበርና ታዳጊውን የቄስ ትምህርት እንዲማር አስገቡት። የቄስ ትምህርት ቤት በነበረበት ወቅት በቀለም አቀባበሉ ጎበዝ እንደነበር አስተማሪው አለቃ ለማ ይናገራሉ። ምስክርነታቸውን ሲሰጡ አስራት በልጅነት በጣም ጎበዝ በመሆኑ ዓመት ሳይሞላው ወንጌሉን ከቁጥሩ አንበልብሎ፤ ከፍካሬ እስከ ነቢያት ደግሞ ድቁና ተቀበለ ይላሉ።

ከቄስ ትምህርቱ ጎን ለጎን ድሬዳዋ ይገኝ ከነበረው ፈረንሳይ ሚሲዮን ገብቶ ቀለም መቁጠር ጀምሮም ነበር። የእናቱ አባት ቀኛዝማች ጽጌ ወረደወርቅ ታዋቂ አርበኛ ነበሩ። ቀኛዝማች ጽጌ ከሶስት ዓመት ተኩል እስር በኋላ ሐገራችን ነጻ ወጥታ ወደ ኢትዮጵያ ሲመለሱ አስራትን አዲስ አበባ አስመጥተው በ1934 ዓ.ም ተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤት አስገቡት። በትምህርት ላይ ጥሩ አቀባበል ሰለ ነበራቸው ከተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤት አጠቃላይ ተማሪዎች አንደኛ በመውጣት የካሜራ ተሸላሚ ነበሩ። በወቅቱ የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ ወጣቶች መካከል ላቅ ያለ ውጤት ያስመዘገቡትን ተማሪዎች ወደ ውጭ ሐገር ልኮ ማስተማር ተጀምሮ ነበርና አስራትም በዚሁ የትምህርት ዕድል ምክንያት ግብጽ ወደሚገኘው የእንግሊዞች ቪክቶሪያ ኮሌጅ ተላከ። በግብፅ አሌክሳንድርያ ቪክቶሪያ ኮሌጅ በ1946 ዓ.ም በቀዶ ጥገና ሙያ በጥሩ ነጥብ ተመርቀው ወጡ። ፕሮፌሰር አስራት ወደ ሌላ አገር ሳይሄዱ ህዝባቸውን ለማገልገል ወደ አገራቸው ተመልሰዋል። ለተከታታይ 5 ዓመታት ህዝቡን ሲያገለግሉ ቆይተው ወደ ስኮትላንድ ኤድንበርግ ዩኒቨርሲቲ የበለጠ ትምህርት ለመማር ሄደዋል። ትምህርታቸውን እንደጨረሱ ሀገር ቤት ከረጅም ጊዜ ልፋት በኋላ የሙያ አጋሮቻቸው ጋር በመሆን የመጀመርያዉን የህክምና ትምህርት ቤት አቋቁመዋል። በሙያቸው መምህር፣ ሀኪምና የትምህርት ቤቱ ዲን ሆነው ደሀው ህዝባቸዉን አገልግለዋል።

ፕሬፌሰሩ ሀኪም ሆኖው ሲሰሩ የሚያሳይ ፎቶ
በቀዶ ጥገና ህክምና ዘርፍ አስራት የመጀመሪያው ኢትየጵያዊ ሐኪም ሆነ። ከዚህ በኋላ አስራት በእድሜም በማዕረግም እያደገ ስለሆነ አንቱ አያልን አንናገራለን። እነ ዶክተር አስራት እስኪተኩት ድረስ የሀገራችን የህክምና ዘርፍ በነጮች የተያዘ ነበር። ዶክተር አስራት ከጓደኞቻቸው ጋር በመሆን የህክምና ማሰልጠኛ እንዲከፈት በመወትወታቸው ምክንያት የጥቁር አንበሳን ሆስፒታል እውን አደረጉ። የጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ሲቋቋም የቴክኒክ ኮሚቴውን የመሩት ዶክተር አስራት ነበሩ። እ.ኤ.አ በ1965 ዓ.ም የጥቁር አንበሳ ሆስፒታል እውን ሲሆን ዶ/ር አስራት ተባባሪ ፕሮፌሰር በመሆን የመጀመሪያ ኢትዮጵያዊ ዲን ሆኑ። በደርግ ወቅትም በካድሬዎች ይደረግባቸው የነበረውን ከፍተኛ ጫና ተቋቁመው ሐገራቸውን ሳይለቁ ህዝባቸውን ሲያገለግሉ ቆይተዋል።

በወቅቱ በተደጋጋሚ ወደ ዘመቻ የተላኩ ሲሆን፤ የሄዱበትን ዘመቻም በክብር ለመወጣት በቅተዋል። በዚህም መሠረት በ1968 ዓ.ም በቀዶ-ጥገና ሐኪምነት በቃኘው ሆስፒታል፣ አስመራ፤ በ1969 ዓ.ም በድጋሚ በቃኘው ሆስፒታል፣ አስመራ፤ በ1970 ዓ.ም በራዛ ዘመቻ በቀዶ-ጥገና ሐኪምነት እና ቡድን መሪነት በመቀሌ ሆስፒታል፤ እንዲሁም በሰኔ 1971 ዓ.ም በቀዶ-ጥገና ሐኪምነት ምጽዋ ዘምተው ግዳጃቸውን ተወጥተዋል። በህክምናው ዘርፍ አስራት የተባለ ጸበል ፈልቋል እስከመባል የደረሰ አንቱታን ያተረፉ ብቁ ሐኪም ነበሩ። ኢህአዴግ በብቃት ማነስ በሚል ከሌሎች 41 ምሁራን ጋር ከአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ በ1985 ዓ.ም እስከሚያባርራቸው ድረስ ዩንቨርስቲውን በትጋት ያገለገሉ የሐገር ባለውለታ ነበሩ። በሙያቸው የተለያዩ ሽልማቶችን ያገኙ ሲሆን፤ ጥቂቶቹን ለመዘርዘር ያክል
►የኢትዮጵያ የክብር ኮከብ የፈረሰኛ ደረጃ
►የዳግማዊ ምኒልክ ኒሻን የፈረሰኛ ደረጃ
►የአብዮታዊ ዘመቻ ዓርማ
►ዓለም አቀፍ የወርቅ ሜርኩሪ (በግል አስተዋጽኦ)
►የቀይ ባህር ኒሻን አንደኛ ደረጃ ይገኙበታል።

ምንም እንኳ አስራት ከደርግ ጋር ሆድና ጀርባ ሆነው የቆዩ ቢሆንም ህወሀት አዲስ አበባን በግንቦት ወር 1983 ዓ.ም ሲቆጣጠር እፎይታ፣ አዲስ ዘመን፣ ማለዳ እና አብዮታዊ ዴሞክራሲ የተባሉት ጋዜጦችን በመጠቀም ከደርግ ጋር ወግነው እንደወጉት ስም ማጥፋት ጀመረ። ፕሮፌሰር አስራት ስለ ተባለው ጉዳይ ሲጠየቁ ግን "እኔ የህዝብ ልጅ ነኝ፤ በሙያዬ ከንጉሡ እስከ መንግሥቱ ቤተሰቦች፣ ከድሀ ገበሬው እስከ ወታደር፤ የሙያዉን ስነምግባር በሚጠብቅ ሁኔታ አገልግያለሁ። እነሱ እንደሚሉት ሳይሆን ምፅዋ ላይ የኢትዮጵያ ወታደር ወይም የተገንጣይ ሳንል አክመናል። አሁንም ቢሆን እርዳታዬ ካስፈለጋቸው ለማገልገል ዝግጁ ነኝ"ነበር ያሉት።

እኚህ ፕሮፌሰር ለየት የሚያደርጋቸው ስብእና በሙያው እንዳሉ ሌሎች አጋሮቻቸው የራሳቸው የግል ህክምና ተቋም ገንብተው ገንዘብ ለመሰብሰብ አንድም ቀን ያልሞከሩ ይልቅም ሕይወታቸውን በሙሉ ለሕዝብ ችግር አሳልፈው የሰጡ መሆናቸው ነው። ወደ አማራው ፖለቲካ ያስገባቸውም ይሄው ስብእናቸው ነበር። በሰኔ መጨረሻ 1983 ዓ.ም በአውሮፓውያን እና አሜሪካ አቀናባሪነት የተደረገው የብሄራዊ ሰላም ጉባኤ ላይ ፕሮፌሰሩ የከፍተኛ ትምህርት ትቋማትን ወክሎ የታደመው ቡድን አባል ሆነው ተሰብስበው ነበር። በዚህ ስብሰባ ላይ የተለያዩ ብሄሮች የወከሉ ቡድኖች ሲኖሩ በህዝብ ብዛቱ ትልቅ የሆነው አማራ አልተወከለም ነበር። የስብሰባው ዋነኛ አጀንዳ ስለ ተጨቆኑ ብሄር ብሄረሰቦች ሲሆን ጨቋኝ ሆኖ የቀረበው ብሄር አማራው ነበር። አገዛዙ በሚቆጣጠራቸው ሚዲያዎች አጋፋሪነት አማራው ደርግና የአፄው ስርዓት ላጠፋቸው ጥፋቶች ሁሉ እንደ ዋና ባለቤት ተደርጎ ተወሰደ ቋንቋው ቆሻሻ ቋንቋ ወይም እንደ ኦነግ አጠራር afan ajawa ተብሎ ይጠራ ጀመር። በግልፅም የወቅቱ ጠቅላይ ሚንስተር ታምራት ላይኔ ሳይቀር ኤርትራ ሄዶ በአማራው ስም ይቅርታ እጠይቃለሁ የሚል ሰንፋጭ ንግግር አድርጎ መጣ። ሳይውል ሳያድር ይሄ በሬ ወለደ ፕሮፖጋንዳ ፍሬ አፍርቶ ወደ ተግባር ተለወጠ።

ይህንን የቃላት ጦርነት ወደ ተግባር ለመለወጥ ሁሉም ታጣቂ ሀይሎች ተንቀሳቅሰዋል። በኦነግ፣ በኦህዴድ፣ በኢህአደግ አማካኝነት በበደኖ 154 ሰው ጊራዋ፣ ኩርፋ ጨሌ፣ ለንጋ፣ ኬርሳ፣ ሶካ፣ ደደር፣ ሂርና፣ ቁኒ፣ መስላ፣ ጋሊቲ፣ ደባ የተባሉ አከባቢዎች ከ1000 ሰው ባላይ አርባ ጉጉ ላይ ከሞተው ውጭ ከ32,000 በላይ አማራ ከመኖራያው ተፈናቅሏል። አርሲ ነገሌ 60 ሰው ወለጋ ከ200 አማሮች በላይ እንደ ዱር እንስሳ ታድነው ተገድለዋል። ይህ ከብዙ በጥቂቱ ነው። ሴቶችን መድፈር ፅንሳቸዉን በጩቤ እያወጡ ማሳየት ዋና ስብእና የጎደላቸው ድርጊቶች መፈፀም መደበኛ ድርጊቶች ነበሩ። ይህ ሁሉ ሲሆን ህወሀት ዳር ቆሞ ለኦነግ እና ሌሎች መሳርያ እያስታጠቀ ያልታጠቁ ንፁሃን ገበሬ አማሮችን አስጨፈጨፈ ነበር። የሚገርመው በቀደመ ስሙ ኢህዴን የጥምቀት ስሙ ብአዴን የሚባለው ደደብ ድርጅት ይህ ሁሉ ጭፍጨፋ ሲካሄድ አንድም ተቃውሞ አላደረገም።

እንግዲህ ከላይ በተጠቀሱ ምክንያቶች እና ሌሎችም ተጨምረው ነው ፕሮፌሰሩን መአሕድን(የመላው አማራ ሕዝብ ድርጅትን) በጥር 1984 ዓ.ም ሊያቋቁም ያስቻለው። መአህድ ገና ከጅማሮው በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ፅህፈት ቤት ከፍቶ በመንቀሳቀስ ተፅዕኖ ማድረግ ጀመረ። በታህሳስ ወር 1985 ዓ.ም ብቻ ከ40 በላይ የመአሕድ ማእከላዊ ኮሚቴ ታስረዋል ፕሮፌሰር አስራት ከአርባ አንዱ የዩኒቨርሲቲ መምህራን ጋር በአቅም ማነስ በሚል ፖለቲካዊ ስም ማጥፋት ታርጋ በገነት ዘውዴ በሚመራው ትምህርት ሚኒስተር አማካኝነት ተባረዋል።

በ1986 ዓ.ም አስራት ደብረ ብርሀን ስብሰባ ላይ ባደርጉት ንግግር አማካኝነት ህወሀት መንግስትን በኃይል ለመገልበጥ አሲረዋል ሲል ሁለት ዓመት ተኩል እስራት ፈረደባቸው። እዛው እስር ላይ እያሉ በ1987 ዓ.ም እንደገና በሌላ ክስ ሶስት ዓመት ጨመረባቸው። ይህ ሁሉ የሚሆነው ከ65 ዓምት በላይ የነበሩ አዛዉንት ላይ ነበር። አስራት ከዚህ ዓመት በኋላ ግን ጤና አጡ በተከታታይም በሀኪሞች የውጭ ህክምና ያስፈልጋቸዋል ቢባልም አገዛዙ ሊቀበል አልፈለገም። በመጨረሻ ከተዳከሙ በኋላ በታህሳስ ወር 1991 ዓ.ም ወደ ውጭ ሄደው ከ5 ወር በኋላ ግንቦት 1991 ዓ.ም በፊላደልፊያ አሜሪካ አረፉ።

የፕሮፌሰሩ አስከሬን ታላላቅ እንግዶች፤ ቤተሰቦቻቸውና አድናቂቆቻቸው በተገኙበት ግንቦት 15 ቀን ወደ ኢትዮጵያ አሸኛኘት ተደርጎለት ከዋሽንግተን ዲሲ ጉዞ ጀመረ። ግንቦት 15 ቀን 1991 ዓ.ም የተነሳው የፕሮፌሰሩ አስከሬን ሮም አርፎ ግንቦት 17 ቀን 1991 ዓ.ም ከቀኑ 11፡30 ላይ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ደረሰ። በስፍራው ሲጠባበቅ የነበረው ህዝብ አስከሬኑን በከፍተኛ አጀብ ለገሐር ወደሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው አደረሰው። በመኖሪያ ቤታቸውም ሌሊቱን ጸሎተ ፍትኃት ሲደረግ አድሮ በማግስቱ አስከሬናቸው በመሠረቱትና በኋላም በሞቱለት ድርጅታቸው፣ መአህድ ጽ/ቤት ጥቂት ቆይታ ካደረገ በኋላ ወደ ቅድስት ስላሴ ካቴድራል አመራ። በቅድስት ስላሴ ካቴድራል ፍትሃትና ጸሎት ከተደረገላቸው በኋላ ቅድስት ስላሴ እንዳይቀበሩ መንግስት በመከልከሉ ምክንያት ግንቦት 17 ቀን 1991 ዓ.ም በባለወልድ ቤተክርስቲያን እንዲያርፉ ተደረገ። ይኸው ላለፉት 18 ዓመታት በባለወልድ የቆየው አጽማቸው ዛሬ ወደሚገባው ቦታ ወደ ቅድስት ስላሴ ካቴድራል ሊዛወር ችሏል። ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ የሁለት ወንዶች ልጆች አባትም ነበሩ።



ምስል :- የፕሮፌሰሩ ፎቶዎች በተለያዩ ጊዜያት


ቪዲዮ፦ ፕሮፌሰር አሥራት ወልደየስ ያደረጉት ንግግር




ይህ ከስር ሊንኩ የተያያዘው ጋሻው መርሻ የጻፈው ነው። መጽሐፉን በማውረድ እንድናነበው ለማለት እንወዳለን።

አንጸባራቂው ኮከብጋ(ጋሻው መርሻ እንደጻፈው)

የአማራ ትስስር በቻይና

ግንቦት 6 ቀን 2014 ዓ.ም

ቻይና

የአማራ ትስስር በቻይና(ANiC)

የአማራ ሕዝብ የሚያኮራ ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ስነጽሑፍ፣ ሃይማኖትና ባህል ያለው፤ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ቅርሶች ባለቤት የሆነ፤ ሃገር የሰራ፣ ነጻነቱን ያስጠበቀ፤ የራሱ የሆነ ፊደል ያለው፤ የጥንታዊ ትምህርት ስርዓት ባለቤት የሆነ ጀግናና ኩሩ ሕዝብ ነው። የአማራ ሕዝብ በሃገረ መንግስት ምስረታ ሃገርን ከወራሪ መጠበቅና ዳር ድንበሯን በማስጠበቅ ታላቅ ገድል በመስራት እኛ ልጆቹ ቀና ብለን እንድንሄድ አድርጎናል።

1 Comments

  1. ታሪክ ክፍሎች እናመሰግናለን። በርቱልን።

    ReplyDelete
ቀዳሚ ገጽ ተከታይ ገጽ
hi