ይህ የአማራ ትሥሥርር በቻይና ይፋዊ ድረ-ገጽ ነው። በዚህ ድረ-ገጽ የአማራን ሕዝብ ታሪክ፣ ሃይማኖት፣ ባሕል፣ ልማድ፣ አርበኝነት፣ ቅርስ እና ሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮችንም ጭምር ለአባላት በሚገባ እናሳውቃለን። የድረ-ገጹ ዋና አላማ የአማራን ታሪክ በሚገባ ለሁሉም በማስተማር ታሪካችንን ወደቀደመ ልዕልናው መመለስ ነው። አንድ አማራ ለሁሉም አማራ፤ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ፤ አንዲት ነጻ ሃገር ኢትዮጵያ -->

የርዕሰ አድባራት ወገዳማት ተድባበ ማርያም ታሪክ

አምሐራ ሳይንት

አምሐራ ሳይንት በደቡብ ወሎ ዞን የሚገኝ ከዞኑ በስፋቱ የመጀመሪያ እንደሆነ የሚነገርለት ቦታ ነው። ቦታው እጅግ ሰፊ ከመሆኑ የተነሳ በአሁኑ ሰዓት ለሁለት ወረዳዎች ተከፍሏል። እነርሱም፦
1. መሐል ሳይንት ወረዳ እና 2. ሳይንት አጅባር ወረዳ ናቸው።
አምሐራ ሳይንት በአማራ ክልል እምብርት በመገኘቱ ደቡብ ወሎ እና ምስራቅ ጎጃም እንዲሁም ከበጌምድር ግዛት ደቡብ ጎንደር ያዋስኑታል። ጎንደር ስማዳ ወረዳ በበሽሎ ወንዝ፤ ጎጃም እነብሴ ሳር ምድር/ መርጡለ ማርያም ወረዳ በአባይ ወንዝ፤ ወሎ በመቅደላ፣ በተንታ እና ለጋምቦ ወረዳ እንዲሁም ደብረሲና እና ቦረና ወረዳዎች ያዋስኑታል። ከሸዋ ደግሞ በመርሃቤቴ በቅርብ ርቀት ላይም ይገኛል። አካባቢው በታሪክ የአማሮች መገኛ አማረኛ ቋንቋን የፈጠሩ ጠበብቶች ቅኔን የደረሱ ሊቃውንት ዜማን ያመለከቱ የዜማ ከያንያን የነበሩበት የአብርሃ ወአፅብሃ ቤተ መንግስት የሚገኝበት የአፄ ይኩኖ አምላክ የፍርድ አደባባይ የአፄ ገላዉዴዎስ መናገሻ የእነ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ሀገር ነች። ጀግኖች ራሶችና ፍታውራሪዎች የነበሩባት በጦር በጎራዴ ሀገርን፣ ታሪክን እና ቅርስን ሲጠብቁ የኖሩባት የአርበኞች ሀገር ነች። አምሐራ ሳይንት የሰሜን ኢትዮጵያ ማዕከል የነበረች ለሀገራችን ኢትዮጵያ ቁልፍ ቦታ ነበረች። ጎንደር በጌምድር ላይ የነበረው የኢትዮጵያ ቤተ መንግስት ከሰሜን ኢትዮጵያ ከለቀቀ በኋላ ሀገራችን ኢትዮጵያም በዘመነ መሳፍንት ከተከፋፈለች በኋላ የኢትዮጵያ ታሪካዊ ምድር አምሐራ ሳይንት ጎስቋላ ሆና አስተዋሽ አጥታ እናት የሌለው ልጅ መስላ በመከራና በሰቆቃ በጨለማ ውስጥ የምትኖር ቦታ እንደነበረች ታሪክ ያስረዳል። አምሐራ ሳይንት ጎጃም፣ ጎንደር፣ ወሎ እና ሸዋ የአራቱም ዞኖች የሚገናኙበት ብቸኛ ማዕከል ነች። ቦታው የዓለም አቀፍ የጥንተ ስልጣኔ መመዘኛ መስፈርቶች ተሟልተው የሚገኙበት ነው። ከነዚህም መካከል ለአብነት የሚከተሉትን እንመልከት፦
1. ሃይማኖት፦ የኦሪት መስዋዕት ይሰዋበት የነበረ በዘመነ ክርስትና የሐዲስ ኪዳን ማዕከል ሆኖ የቀጠለ ነው።
2. ቋንቋ ፦ አማርኛ ቋንቋ የተፈጠረበት ምድር ነው።
3. ዜማ ፦ የዘመነ ብሉይ የአምልኮ መፈፀሚያ ዜማ የነበረበት ፣ በዘመነ ሐዲስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የሰዓታት ዜማ የደረሱበት ቦታ ነው።
4. ፍልስፍና ፦ ዮሐንስ ገብላዊ ቅኔ ደርሶ ያመለከተበት ቦታ ነው።
5. ትምህርት ፦በጽሑፍ ቋንቋ የአብነት ትምህርት ይሰጥበት የነበረ ቦታ ነው።
6. የመንግሥት አስተዳደር ፦ እንደ ክብረ ነገስት ያለ የሥርዓተ መንግሥት መምሪያ ቦታና መዋቅር የነበረበት አስገራሚ ቦታ ነው።
7 . የሐይማኖት እና የፍልስፍና ፣ የኪነ ጥበብና የስነ ጥበብ ድርሰቶች ያሉበት ቦታ ነው።
8 . የግዕዝ፣ የአረማይክ፣ የአማርኛ ጽሑፎች በብራና እና በድንጋይ ላይ ታትመው የሚገኙበት ቦታ ነው።
9. የጥንት ዘመን የጦር መሳሪያዎች እና የግብርና መሳሪያዎች፣ የእንስሳት እርባታና የሰብል ማምረቻ ጥንታዊ መገልገያዎች የሚገኙበት ቦታ ነው።
10. ስነ ህንጻ ፦ ከክርስቶስ ልደት በፊት የጥንት የስነ ህንፃ አሻራዎች፣ የአምልኮ መሰዊያ ቦታዎች፣ ሌዋውያን በእስራኤል ይሰሯቸው የነበሩ የሰቀላ ቤት አምሳያዎች ያሉበት ቦታ ነው።
በጠቅላላ አምሐራ ሳይንት የጥንት ፐርሺያ፣ ቻይና፣ ግብፅ እና ግሪክ የመሳሰሉት በስልጣኔ የተለኩበት በአገራችን የአክሱም ስልጣኔ የተገለጠበት ሁሉ ሳይጓደል ተሟልቶ የሚገኝበት ግን እስከ ዛሬ ታሪኩ ተዳፍኖ የኖረ ስፍራ ነው።

ተድባበ ማርያም

ተድባበ ማርያም ማለት ለእግዚአብሔር የተመረጠ ከፍተኛ ቦታ ማለት ነው። በዚህ አስገራሚ ስፍራ በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት በአምሐራ ሳይንት ወረዳ የምትገኘው ጥንታዊቷ ርእሰ አድባራት ወገዳማት ተደባበ ማርያም የተመሰረተችው በዘመነ ብሉይ በቃዳማዊ ምኒልክ ዘመነ መንግስት በ982 ዓመተ ዓለም(ከኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በፊት) ነው። ርእሰ አድባራት ወገዳማት ተደባበ ማርያምን የመሰረታት የቤተልሔም ተወላጅና የአሚናዳብ ዘር የሆነው ሳቤቅ ነው። አመሠራረቷም በመፅሐፈ ሱባኤ ዘአማኑኤል ካልእ ላይ እንደተጻፈው ሌዋዊያን ካህናት ከእስራኤል በአዛሪያስ መሪነት የጁን አልፈው ከዛሬዋ አምሐራ ሳይንት ደረሱ። 12 በሮች ባለው ተራራ ላይ ለእግዚብሔር ቤተ መቅደስ ከሰሩ በኋላ ግማሾቹ "ደብር ደባብ" እንበላት አሉ አዛርያስ እና የዳዊት የወንድም ልጆች ሳቤቅ ይህቺማ የኢየሩሳሌም የዳዊት መታሰቢያ ከተማ ትሆን ዘንድ ተድባበ ጽዮን እንበላት ብለው እንደሰየሟት ይነገራል።

አሥራ ሁለቱ የተድባበ ማርያም በሮች ዝርዝር

⇛ ፊት በር

⇛ የጌላት በር

⇛ የታንኳ በር

⇛ አምጣ ፈረሴን በር

⇛ ግራዢ በር

⇛ ገተም በር

⇛ አቅቻ በር

⇛ ፈረስ መጣያ በር

⇛ ቦካ በር

⇛ ጨረር በር

⇛ የጎድ በር

⇛ መርገጫ በር

በብሉይ ዘመን መስዋዕተ ኦሪት ከተሰዋባቸው መካከል አክሱም ጽዮን፣ ተድባበ ጽዮን (የዛሬዋ ተድባበ ማርያም)፣ መርጡ ለማርያም፣ ጣና ቂርቆስ ቀዳሚዎቹ ናቸው፡፡ ቀዳማዊ ምኒሊክ ከአባቱ ከንጉሡ ከሰሎሞን መንግስት ተቀብሎ ከኢየሩሳሌም ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ 4 መናብርት ጽዮን ይዞ እንደመጣ ታሪክ ይናገራል። እንደ ኦሪቱ ስርዓት መናብርቱን ሲያፀናም፦
1. የአክሱም ጽዮን (ንቡረ እድ)
2. የተድባበ ማርያም (ፓትርያርክ)
3. የመርጡለ ማርያም (ርዕሰ ርኡሳን)
4. የጣና ቂርቆስ (ሊቀ ካህናት) ተብለው ተሰየሙ።
ከቀዳማዊ ምኒልክ ጀምሮ እስከ ጃንሆይ ዘመነ መንግስት ከሦስት ሺህ ዓመታት በላይ ንጉስ ቀብተው የሚያነግሱ እነዚህ አራቱ መናብርተ ጽዮን ነበሩ።
►የአክሱም ንቡረ ዕድ ማንኛውም ንጉሥ ሲነግሥ ከሥርዓተ ንግሥ በኋላ ዘውዱን በክብር ከራሱ ላይ ያቀዳጃል፡፡
►ተድባበ ማርያም ፓትርያርክ "ቅንት ሰይፈከ ኃያል ውስተ ሐገርከ በሥንከ ወበላሕይከ አርትዕ ተሰራህ ወንገሥ በትረ ጽድቅ ወበትረ መንግስትከ" ብሎ ሰይፈ መንግስቱን ለንጉሥ ያስታጥቀዋል። በትረ መንግስቱን ህለተ ወርቁን ጠላትህን በእጅህ ጭብጥ በእግርህ እርግጥ አድርገህ ግዛ ብሎ በቀኝ እጅ ያሲይዘዋል። በዚህ እውነተኛ ፍርድ ፍረድበት የእግዚአብሔርን ሕግ ጠብቅበት የተበላሸውን አድስበት የታደሰውን አጽናበት አመፀኞችን ቅጣበት ፍቃዶኞችን ሹምበት በዚህ ሁሉ አምላካችንን አገልግልበት ብሎ ይሾመዋል፡፡
► የመርጡለ ማርያም ርእስ ርኡሳን ልብስ መንግሥቱን ያለብሰዋል፡
►የጣና ቂርቆሱ ሊቀ ካህን… ቅብአ ንግሥናውን ይቀባል
ይህ ሁሉ ሥርዓት የሚደርሰው 40 ቀን ለሥርዓተ ንግሥ የተወሰነው ከብሉይና ከሐዲስ ኪዳን የተውጣጣው ጸሎትና መሥዋዕት ካረገ በኋላ ነው። በእነዚህ አራት መናብርተ ጽዮን ያልነገሠ ንጉሥ ጠላት አጥፍቶ፣ አገር አስፍቶ እና በሃይማኖት ፀንቶ ሊኖር አይችልም። እነዚህ ባሉበት ከነገሠ ግን ሀገር ለመጠበቅና ሁሉን ነገር ለማድረግ ይቻለዋል። ይኸውም ከቀዳማዊ ምኒልክ ሲያያዝ መጥቶ እስከ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ድረስ በእነዚህ 4 መናብርተ ጽዮን ግርማዊነታቸው ነግሠው 43 ዘመን ያለምንም እንከን ገዝተዋል። ግርማዊነታቸው ሲነግሡ የነበሩት የርእሰ አድባራት ወገዳማት አሰተዳደሪ ለግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሰይፈ መንግሥትና ህለተ ወርቅ ያስጨበጡና ያስታጠቁ ፓትርያርክ አፈወርቅ ይባሉ ነበር። የመናብርተ ጽዮኑ ስያሜም 3ቱ በእመቤታችን ምሳሌ በጽዮን ስም አራተኛው የሊቀ ካህናቱ ታቦት ቅዱስ ሚካኤል ነው። ከእነዚህ ጋር ቀዳማዊ ምኒልክን ተከትለው ወደ ኢትዮጵያ የመጡ 12,000 መሣፍንትና መኳንንት ወይዛዝርት 1,500 በተግባረ ዕድ የሰለጠኑ የወርቅና የብር፣ የብረትና የመዳብ፣ እንዲሁም የነሐስ አንጥረኞች አዋቂዎች ጠቢባን ፀበርተ ዕፀውና ወቀርተ አዕባን ናቸው። እነዚህ ኢትዮጵያ ገብተው በየክፍለ ሀገሩ ሥራቸውን ሲጀምሩ አክሱም ጽዮን ትግራይ ላይ ስትቀር የዳዊት የወንድም ልጅ ሳቤቅ የሰሎሞን አጎት ከመጀመሪያው ፓትርያርክ አዛሪያስ ጋር ተከዜን ተሻግሮ አምሐራ ሳይንት ደረሰ። የአሁኗ ተድባበ ማርያም ካለችበት አምባ ላይ ሲደርስ ቤተ እግዚአብሔር መሥራት ጀመረ። ቦታዋንም በሀገሩ ስም ገሊላ ብሎ ጠራት። ፓትርያርክ አዛሪያስ ደስ አለውና ስሙን በቡራኬ አፀደቀለት። ለዚህችውም ተድባበ ጽዮን ቤተ መቅደሱን ሰርቶ ሲጨርስ ከሌዋውያኑም ከካህናቱም ከፍሎ መስዋተ ኦሪት የሚሰው ካህናትና ሌዋውያንንም ሾመ። መስፍኑ ሳቤቅ ቤተልሄማዊም በገፀ ንጉስ በወርቅ ወንበር የሚቀመጥ ነበር። ከዚህ ላይ ገሊላ ብሎ ከሰየመ በኋላ አገሮቹን አሻግሮ እያየ በሀገሩ ምሳሌ ይሰማቸው ጀመር። ደብረ ዘይት፣ ኬብሮን አሁን ከቀን ብዛት የተነሳ ህዝቡ ኬብሮንን ከሚኖር ይለዋል ይኽውም ከተድባበ ማርያም አምባ በር ወደ ምስራቅ ያለውን መግቢያ ነው። ወደ ቀኝ በኩል ተመልከተና እያሪኮ ትባል አለ ከቀን ብዛት ግን ሕዝቡ እያሪኮን አራሆ ይሏታል ቀጥሎ ኢየሩሳሌም ቀጥሎ ሎዛ ከዚህ ከሎዛ በላይ ታቦር አለው ይኸውም በአፄ በዕደ ማርያም ዘመን መግስት የተነሱት የቅኔ ፈጣሪዎች እነ ዮሐንስ ገብላአዊ፣ እነ ሠምራ አብ፣ እነ ወልደ ገብርኤል እነ ደቅ እስጢፋ የነበሩበት ነው።ከታቦር ቀጥሎ ሊባኖስ፣ ደማስቆ፣ አርሞንኤም፣ ደብር ፋራን፣ ደብረሲና አሁን ቦረና በመባል የሚጠራው ነው። በስተሰሜን በኩል ኮሬብ፣ ቃዴስ ደብረ ፍጌህ፣ ቂሣርያ፣ ቢታኒያ እና ጋዛ ፣ ጎልጎታ፣ ፌልስጥኤም ወዘተ ተብለው ተሰይመዋል። ይኸውም መታሰቢያነቱ ለ12 ነገደ እስራኤል እንደሆነ ይነገራል።
ሥርዓተ በዓላት በተድባበ ማርያም
በዘመነ ኦሪት የቂጣ በዓል የአይሁድ ፋሲካ ይከበር ነበር። ወደ ኢትዮጵያ ታቦተ ጽዮንን ተከትለው ከመጡት አስራ ሁለት ሺህ ነገደ እስራል ሁለት ሺህ አመስት መቶዎቹ ተድባበ ማርያም እንደገቡ ይነገራል። ዘመነ ኦሪት አልፎ በክርስቶስ ልደት ዘመነ ሐዲስ እንደተተካ በ337 ዓ.ም በቅዱሳን ነገሥታት አብረሃ ወአጽበሃ ዘመን ተድባበ ጽዮን የሚለው የምሳሌ ስም አልፎ በአማናዊነት ድንግል ስም ተድባበ ማርያም ተባለች። ነገሥታቱ አብርሃ ወአጽብሃም የኦሪታዊት ተድባበ ማርያምን ክብር ከፍ በማድርግ ለሥርዓተ ቁርባንና ለሐዲስ ኪዳን ለተዋሕዶ ሃይማኖት መሰረት ትሆናቸው ዘንድ 318 መዘመራን ካህናትና ዲያቆናት ከካህናተ ኦሪቱ ጋር ያለውን ሐዲስ ኪዳን የሚያስተምሩ መምህራን ተክለው ከቀዳሚው ምኒልክ ዘመን በሚልጥ ክብር አክብረው እንበረምን ህዝበ ቀደስ አሰኝተው በፍሬምናጦስ አባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ሥልጣን አጽንተው የተደባበ ማርያም ክብር እስከ አሁን ድረስ የቆየውን ማዕረግ የመሰረቱ እነሱ ናቸው። በአብረሃ ወአጽብሃ ዘመን መንግሥት የነበረው ፓትርያርክ መርሐ ጽዮን ሲሆን በአጼ ካሌብ ዘመን የነበርው ፓትርያርክ ደግሞ ፓትርያርክ ዘሙሴ ይባላል። እንዲህ ሆኖ ሲያያዝ ታሪክ መጣና ከአጼ ገላውዴዎስ ዘመነ መንግስት ሲደርስ የግራኝ ወረራ ተነስቶ አድባራቱን ሁሉ ሲያጠፋ የተድባበ ማርያም ደብር ክብር ምንም አልተደፈረም። አንዳንድ ፀሐፊዎች ግን እርግጠኛ ካልሆነ ታሪክ በመነሳት ገና በይሆናል "ግራኝ ተድባበ ማርያምን አቃጥሏታል" በማለት ጽፈዋል። እንዲያውም በዘመኑ የነበረው ፓትርያርክ አባ ዮሐንስ የተድባበ ማርያምን ጽላት ይዞ ዘምቶ አጼ ገላውዴዎስ ጋር ግራኝን ድል ነስቷል። በዚህም ጦርነት ጊዜ በበጌ ምድር አፈረዋናት ያለው የመካነ ሰማዕት ገላውዴዎስ ጽላትም ግራኝን ድል በማድረግ ተመስርቷል። ከዚህ በኋላ አጼ ጋላውዴዎስ አብርሃ ወአጽብሃ በተደባበ ማርያም በሰጡት ክብር ልዕልና ጨምሮ ከአባይና ከበሽሎ ከጎንደር በር አንስቶ በጠቅላላ በወሎ ምድር እስከ አዳል ነጭ ሣር ድረስ ለተድባበ ማርያም መተዳደሪያ ሲሶ መንግሰት ሰጥቷል፡፡ አብረሃ ወአጽብሃ ተድባበ ማርያምን አንጽው ካበቁ በኋላ ጥር 21 ቀን በዓሏን ለማክበር ደንግገው እንደነበር ታሪክ ምስክር ነው። ይህም የበዓል አከባበር እስከ ዐፄ ገላውዴዎስ ከቆየ በኋላ ዐፄ ገላውዴዎስ ግራኝ አህመድን ድል አድርጎ ሲመለስ ግንቦት ፩ ቀን ተድባበ ማርያም በመግባቱ የገባሁት በልደቷ (እለቱ የእመቤታችን ልደቷ ነው) በማለት የልደታን ጽላት አሰገብቶ የተድባበ ማርያምን በዓል ግንቦት ፩ ቀን እንዲሆን አዋጅ አስነገረ። ከዚያን ዘመን ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ ግንቦት አንድ ቀን በደማቅ እና በልዩ ሁኔታ ይከበራል። በማግስቱ ግንቦት ሁለት የገላውዴዎስ ልደት በመሆን ተከብሮ ይውላል። ዋዜማው ከጧቱ ሦስት ሰአት ተጀምሮ ከቀኑ አስር ሰአት ያልቃል ማህሌቱ ማታ ሁለት ሰአት ተጀምሮ እስከ ቅዳሴ መግቢያ ይቀጥላል። በማህሌት ሰርዓቱ ላይ የሚቆመው እንደሌላ ቦታ መልክዓ ማርያም ሳይሆን የራሷ ሊቃውንት የደረሱት መልከዓ ልደታ ነው። ለአብነት ያህል፦ ሰላም ለህንብርትኪ ዘአርያሁ ሰሌዳ ወለ ማህጸንኪ ቤቴል ማህደረ ክርስቶስ እንግዳ በእንቲአኪ ይብሉ ማርያም ሠራዊተ ንጉስ ይሁዳ ዳዊት ዘመዳ ኤያቄም ወለዳ ኤያቄም ወለዳ ዳዊት ዘመዳ። እያሉ የራሷን ድርሰት ይቆማሉ። ይህም በሌላ ቦታ አይባልም። ከክብረ በአሏ በተጨማሪ ከዓመት እስከ ዓመት ሰብሐተ ነግህና ሰዓታት ቅዳሴና መዓልት ሰዓታት አይቋረጥባትም። ሁልጊዜ የሚቀድሱት 7 ልዑካን ሲሆኑ አመራረጣቸውም 20 ዓመት ያልሞላቸው 4 ሕፃናት ዲያቆናትና 3 አበው መነኮሳት ሆነው ነው። ገዳሟ ውስጥ 2 የንባብ፣ 2 የቅኔ፣ 4 የድጓ፣ 2 የአቋቋም፣ የዝማሬ መዋስዕትና የቅዳሴ ጉባዔያት አሏት። አሁን በሌላው ደብር ዓመት እስከ ዓመት ይቀድስ ነበር፣ ሰብሐተ ነግህ ይቆምበት ነበር ተብሎ ይነገርበታል እንጅ ሲሆን አይታይም ተድባበ ማርያም ግን እስከ አሁን ድረስ ቅዳሴና ስብሐተ ነግህ ሰዓታትና መዓልት ሰዓታት ዓመት እስከ ዓመት አይቋረጥም። ርእስ አድባራት ወገዳማት ተድባበ ማርያም የሐዲስ ኪዳን የስርዓት መነሻ የቅኔ ምንጭ የደጓ ምልክት ነቅ ደጓ ከጠፋ በኋላ የድጓን ምልክት በመፍጠር ለትወልድ ያሰተላልፉ አዛዥ ጌራንና አዛዥ ዘራጉኤልን ያፈራች ዙሪያዋን በታላቅ ገዳማት እና አድባራት የተከበበች የአማርኛ ቋንቋ መገኛ እንደሆነች የሚነገርላት የጎንደር የጎጃምና የሽዋ እንዲሁም የወሎ መገናኛ ማእከል የሆነች ለስነ ልሳን ተመራማሪዎች ትልቅ የቅርስ ስፍራ የሆነችው ርእስ አድባራት ወገዳማት ተድባበ ማርይም የታቦር ተራራ የቅኔ መገኛ ሰማንያ ጋሻ መሬት የሸፈነ የደንቆሮ ብሔራዊ ፓርክ ክልል የሚገኝባት ስትሆን ለኢትዮጵያ ታላቅ የታሪክ ማህደር ናት። ተድባበ ማርያም በዮድት ጉድት አርባ አመት ወረራ፤ በግራኝ አህመድ የአስራ አምስት አመት ወረራ ያልተደፈረች የቅርስ ቦታ ነች። እስከ ሰባት ትውልድ ደጅሽን የረገጠውን ሁሉ እምርልሻለሁ ብሎ እግዚአብሔር ቃል የገባላት የበረከት የቃል ኪዳን ቦታ ነች።
ምስል ፩ ተድባበ ማርያም
የቅርስ ክምችት
ተድባበ ማርያም እድሜ ጠገብና አያሌ ታሪክ ያስተናገደች እጅግ ጥንታዊ መካነ ቅርስ ያለት ናት። በኢትዮጵያ 2ኛ በአምሐራ ክልል 1ኛ ባለ ብዙ ቅርስ፣ የታሪክ የባህልና የእምነት ባለ አደራ ናት። የሚታዩና፣ የማይታዩ፤ ብሎም የተሰወሩና፣ ያልተነገሩ አያሌ ድንቅ የኢትዮጵያ ታሪኮችና ቅርሶችን ጠብቃ ዘመን ያሻገረች ናት። ነገሥታት ዘውዳቸውን አውልቀው የሰጧት፣ ካባቸውን የደረቡላት፣ ደስታቸውን በድንቅ ስጦታዎቻቸው የገለጹላት ስፍራ ናት። አፄ ገላውደወስ፣ አፄ ዘርአያእቆብ፣ አፄ በዕደማርያም፣ አፄ እስክንድርና፣ ንጉሥ ሚካኤልና ሌሎች ነገሥታትም ልብሰ መንግስታቸውን፣ እንቁ፣ አልማዝ፣ ወርቅ፣ ብርና፣ ሌሎች የከበሩ ማእድናትንም ለቤተክርስትያኗ አበርክተዋል። ተድባበ ማርያም እጅግ ብዙ ውድ ሀብቶች አሏት፣ አንዳንዶቹም ከድሮው መጽሐፍ ቅዱስ (ኦሪት) ጀምሮ ናቸው። ክምችቶቹ አሁን በአብያተ ክርስቲያናት ግቢ ውስጥ ባለው ሙዚየም ውስጥ ይታያሉ። እጅግ ልዩ ከሆኑት ቅርሶች መካከልም የበግ ምስልና የተቁለመለመ የበግ ቀንድ ያለበት መስቀል በዚያ ይገኛል፡፡ የዚህ መስቀል ብርሃን የሚያስገርምና ዓይንን የሚያንፀባርቅ ሲሆን ከምን አይነት ማእድን እንደተሰራ አይታወቅም። ከጥንታዊያን ነገስታትም መካከል ዐፄ ካሌብ ወደ ደቡብ አረቢያ የናግራንን ክርስቲያኖች ለመርዳት ሲዘምቱ ፓትርያርክ ዘሙሴ እሱም የኦየሩሳሌምን ገዳም ያቀናና በመጨረሻም በአባ ጴንጠሌዎን ገዳም ገብቶ ያረፈ አባት ጋር ዘምተው ድል አድርገው ሲመለሱ ይዘው የሄዱትን ጋሻ በስዕለት ለተድባባ ማርያም አስገብተውት በቦታው ይገኛል። እንዲሁም የእብራይጥ ሲኖዶስና የአረማይክ ቅዳሴ እግዚእ በቦታው ላይ ይገኛል። በዚህ ገዳም ከ1000 ያላነሱ የብራና ጥንታዊያን መጸሐፍት ይገኛሉ። እነዚህም መጻሕፍት ክፊሎቹ በጥንታዊት የአክሱም ዘመን መንግስት የተጻፈ ሲሆኑ ሌሎቹ ደግም በመካከለኛ ዘመን የተጻፉ ናቸው። ተድባበ ማርያም ለትውልድ ካቆየቻቸው ቅርሶች መካከልም የሚታዩትና የሚዳሰሱት በጥቂቱ ከዚህ በታች ተዘርዝረዋል፦
1. የበግ ምስልና እንደ ኮኮብ የሚያበራ የተቁለመለመ የበግ ቀንድ ያለበት መስቀል
2. ዐፄ ካሌብ ወደ ደቡብ አረቢያ የናግራንን (የመን) ክርስቲያኖች ለመርዳት ይዘውት የዘመቱት ጋሻ
3. የእብራይጥ ሲኖዶስና
4. የአረማይክ ቅዳሴ እግዚእ (ገበታ ቅዳሴ)
5. በአረማክ ቋንቋ የተጻፉ የስሌዳ መጻህፍት
6. 4. በአረበኛና በግእዝ የተጻፉ መጻህፍት
7. ወንጌል ዘወርቅ እየተባለ የሚጠራ ትልቅ የወርቅ ጉብጉብታ ያለበት ቅዱስ ወንጌል
8. የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ጳጳስ የቀደሰበት የእጅ መስቀል
9. የመጥመቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ መስቀል
10. የዕጨጌ ዮሐንስ በትረ ሆሳዕና እና የእጅ መስቀል
11. የአቡነ አኖሪዎስ የእጅ መስቀል
12. የአቡነ ቄርሎስ የእጅ መስቀል
13. ስእርተ ሀና (የማርያም እናት፣ ቅድስት ሀና ጸጉር)፣ የተቀመጠበት የሽክላ ገንቦ ጥንታዊና በስነ-ጥበባዊ ይዘቱ የሚያስገርም ነው
14. ሄሮድስ የጨፈጨፋቸው ህጻናት ዓጽም በክፊል
15. የቅዱስ ጊዩርጊስ አወራ ጣት
16. 13. በአጠቃላይ የ28 ሰማእታት ዓጽም ይገኛል
17. የዐፄ ገላውዴዎስን ጨምሮ የስድስት ነገስታትና የአራት እጨጌዎች ዓጽም ይገኛል
18. የአጼ ዳዊት ዙፋን
19. የቅዱስ የሬድ ድጓ እና ጊዩርጊስ ወልደ አሚድ፣ ገድለ አዳም
20. ከ1000 የሚበልጡ ጥንታዊ የብራና መጻህፍት
21. ሉቃስ እንዳሳላት የሚነገርላት የቅድስት ድንግል ማርያም ስዕለ አድህኖ
22. በርካታ ጥንታዊ የእጅና የመጾር መስቀል
23. 20.ልዩ ልዩ ንዋየ ቅድሳት
24. የነገስታት ዘውዶች፣ወንበርና አልባሳት
25. ባለ 3 ተከፍች የገበታ ስእልና ጥንታዊና ስነ ጥበባዊ ቅርሶች ይገኛሉ
ምስል ፪ ከነገሥታቱ የተበረከቱ በወርቅ ጣፋ እና ሙጣ እንዲሁም በብር እና በወርቅ የተሰሩ ጋሻዎች
ምስል ፫ የተድባበ ማርያም ሀብታት( ጋሻ፣ ጦር እና የእጣን ማቃጠያዎች)
ምስል ፬ ከዓሣ ነባሪ ቆዳ የተሠራው የንጉሥ ዳዊት ዙፋን(መንበረ ዳዊት)
ምስል ፭ በባህላዊ መንገድ በወርቅ እና በቀይ ክፋይ ልብስ(ቬልቬት) ተከብቦ የተሰራ ጃንጥላ
ምስል ፮ ከወርቅ እና ከአልማዝ የተሰራ የንጉስ ሚካኤል ዘውድ
ምስል ፯ አጼ ገላውዴዎስ የተዋጉበት ሳበው ጠመንጃ
ምስል ፰ ንዋ በግዑ ባለሁለት ተካፋች መስቀል
"ነዋ በግዑ" የእጅ መስቀል በመጀመሪያው የኢትዮጵያዊ ጳጳስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን የቀደሰበትና ለተድባበ ማርያም የሰጡት ስጦታ ነው።
ምስል ፱ ቅዱስ ሉቃስ እንደሳላት የሚነገርላት የእመቤታችን ስእል አድህኖ


ታሪካችንን እንወቅ!!



የአማራ ትስስር በቻይና

ሚያዚያ 28 ቀን 2014 ዓ.ም

ቻይና

ስለ ተድባበ ማርያም የተደረገ ጥናት(⬇)
ዶክተር መንግሥቱ ያደረገው ቃለ ምልልስ
የአማራ ትስስር በቻይና(ANiC)

የአማራ ሕዝብ የሚያኮራ ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ስነጽሑፍ፣ ሃይማኖትና ባህል ያለው፤ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ቅርሶች ባለቤት የሆነ፤ ሃገር የሰራ፣ ነጻነቱን ያስጠበቀ፤ የራሱ የሆነ ፊደል ያለው፤ የጥንታዊ ትምህርት ስርዓት ባለቤት የሆነ ጀግናና ኩሩ ሕዝብ ነው። የአማራ ሕዝብ በሃገረ መንግስት ምስረታ ሃገርን ከወራሪ መጠበቅና ዳር ድንበሯን በማስጠበቅ ታላቅ ገድል በመስራት እኛ ልጆቹ ቀና ብለን እንድንሄድ አድርጎናል።

Post a Comment

ቀዳሚ ገጽ ተከታይ ገጽ
hi