ይህ የአማራ ትሥሥርር በቻይና ይፋዊ ድረ-ገጽ ነው። በዚህ ድረ-ገጽ የአማራን ሕዝብ ታሪክ፣ ሃይማኖት፣ ባሕል፣ ልማድ፣ አርበኝነት፣ ቅርስ እና ሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮችንም ጭምር ለአባላት በሚገባ እናሳውቃለን። የድረ-ገጹ ዋና አላማ የአማራን ታሪክ በሚገባ ለሁሉም በማስተማር ታሪካችንን ወደቀደመ ልዕልናው መመለስ ነው። አንድ አማራ ለሁሉም አማራ፤ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ፤ አንዲት ነጻ ሃገር ኢትዮጵያ -->

የታሪክ ጸሐፊው አቶ ተክለፃድቅ መኩሪያ

 ታላቁ ሰው የሀገር ባለውለታ የታሪክ ጸሐፊ አቶ ተክለፃድቅ መኩሪያ 

መስከረም 1 ቀን 1906  ሸዋ በተጉለትና ቡልጋ አውራጃጊናገር ወረዳ፣ በአሳግርት ልዩ ስሙ አቆዳት በሚባል ስፍራ ተወለዱ። ወደ አዲስ አበባ መጥተው የመጀመሪያ ትምህርታቸውን በአማርኛና በግዕዝ ካጠናቀቁ በኋላ በቀድሞ ተፈሪ መኮንን ት/ቤት የፈረንሳይኛ ትምህርት ተምረዋል። ለኢጣሊያ የወረራ ዘመን ሶስት ዓመታት በግዞት በሶማሊያ ቆይተዋል። ከዚያም ኢትዮጵያ ከኢጣሊያ አገዛዝ ነፃ እንደወጣች በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር በአስተዳደርና በዲፕሎማሲ መስክ አገልግለዋል።


 አቶ ተክለፃዲቅ መኩሪያ በኢትዮጵያ የንባብና የትምህርት ዓለም በስፋት የሚታወቁት ፅፈው ባዘጋጇቸው እጅግ ግዙፍ በሚባሉ መፃሕፍቶቻቸው ነው። በቀደመው ዘመን ላይ ለትምህርት ቤቶች የታሪክ መማሪያ በአምስት ቅፅ የታተሙት መፅሐፍቶቻቸው ነበር የሚያገለግሉት። የኢትዮጵያን ታሪክ ከማንም በበለጠ መልኩ የፃፉ ሰው ናቸው። ምክንያቱ ደግሞ እርሳቸው የኢትዮጵያን ታሪክ ለባለታሪኩ ለኢትዮጵያ ሕዝብ በመፃፍ ይታወቃሉ። የእርሳቸው ዘመን ላይ የነበሩ የታሪክ ምሁራንም ሆኑ አሁን ያሉት ምሁራን በአብዛኛው የሚፅፉት በውጭ ሀገር ቋንቋ ነው። እርሳቸው ግን ለኢትዮጵያዊ ወገናቸው ውብ በሆነ የአፃፃፍ ስልታቸው ሲፅፉለት ነበር የኖሩት ።

ከታሪክ ጸሐፊነታቸው በተጨማሪ በመንግሥት አስተዳደር ውስጥ ብዙ አገልግለዋል። ከጣሊያን ወረራ በኋላ ከ1934 ዓ.ም እስከ 1935 ዓ.ም በመዝገብ ቤት ሹምነት እና በሚኒስትር ጸሐፊነት ሰርተዋል። ከ1935-1966 ዓ.ም ደግሞ የምድር ባቡር ዋና ተቆጣጣሪ፣ በፓሪስ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ዋና ፀሐፊ፣ የጡረታ ሚኒስቴር ዋና ዳይሬክተር፣ በረዳት ሚኒስትርነት ማዕረግ የብሔራዊ ቤተመዛግብት ወመዘክር ዋና ኃላፊ፣ በሚኒስትር ማዕረግ በእየሩሳሌም ቆንስል፣ በቤልግሬድ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው አገራቸውን አገልግለዋል። የአፄ ኃይለሥላሴ ስርዓት በኃይል ከተወገደ በኋላም በዘመነ ደርግ እስከ 1967 ዓ.ም አጋማሽ ድረስ የትምህርትና የባሕል ሚኒስትር ሆነው ማገልገላቸውን ታሪካቸው ያወሳል። ከዚያም በጡረታ ተገለሉ።

እኚሁ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ለንባብ ያበቋቸውን የኢትዮጵያን የታሪክ መፃሕፍት በአብዛኛው የፃፉት በመንግሥት ሥራ ላይ እያሉ የእረፍት ግዜያቸውን በመሰዋት ነው። ለሕትመት ከበቁላቸው አያሌ ሥራዎቻቸው መካከል ዋና ዋናዎቹ የሚከተሉት ናቸው። እነዚህም፦ 

                           1. የኢትዮጵያ ታሪክ ከአፄ ቴዎድሮስ እስከ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ፣

                           2. የኢትዮጵያ ታሪክ ከአፄ ልብነድንግል እስከ አፄ ቴዎድሮስ፣

                           3. የኢትዮጵያ ታሪክ ከአፄ ይኩኖ አምላክ እስከ አፄ ልብነድንግል፣

                           4. የኢትዮጵያ ታሪክ ከአክሱም ዛጉዌ እስከ ይኩኖ አምላክ፣

                           5. የኢትዮጵያ ታሪክና ኑቢያ፣

                           6. ከጣኦት አምልኮ ወደ ክርስትና፣

                           7. ጥንታዊት ኢትዮጵያና ግብፅ

                           8. የሰው ጠባይና አብሮ የመኖር ዘዴ፣

                           9. የግራኝ አሕመድ ወረራ

                          10.አፄ ቴዎድሮስ እና የኢትዮጵያ አንድነት

                          11.አፄ ምኒልክ እና የኢትዮጵያ አንድነት እና ሌሎችም ያልታተሙ አያሌ ስራዎች አሏቸው።

ከላይ ከተዘረዘሩት መጽሐፍ ውስጥ የኢትዮጵያ ታሪክ ከአክሱም ዛጉዌ እስከ ይኩኖ አምላክ የሚለውን ከዚህ አውርደው ማንበብ ይችላሉ።

እነዚህ ከላይ የሰፈሩት የታሪክ መፃሕፍት በኢትዮጵያ ውስጥ እንደ ታላላቆቹ ቅርሶች እንደ አክሱም፣ ላሊበላና ጎንደር የሚታዩ እንደሆነ ጸሐፊያን ይናገራሉ። አሁን ያሉ ወጣት ጸሐፊያን የታሪክ መጽሐፍት እያሉ የሚያሳትሟቸው ስራዎቻቸው በአብዛኛው ከአቶ ተክለፃዲቅ መኩሪያ ስራዎች የተገለበጡ ናቸው። የተኮረጁ ናቸው። የተሰረቁ ናቸው። ለአንዳንዶቹ ደግሞ የመነሻ ሃሳብ የሚሰጡ ናቸው። ተክለፃዲቅ መኩሪያ በኢትዮጵያ የታሪክ ፅሁፍ ውስጥ ዘላለማዊ ብርሃን ረጭተው ያለፉ ብርቅዬ ደራሲ ነበሩ። ይህንን ውለታቸውን ያስታወሰ ሌላ አካል ባለመኖሩ  ላዕከ ተክለማርያም ሐምሌ 20 ቀን 1992 ዓ.ም ለተክለፃዲቅ መኩሪያ የሚከተለውን ቅኔ ያቀረቡት።

    

                ያንድ ቤት ያስር ቤት የመቶ ቤት እያልን፣

                የታሪኩን ሂሳብ ገና እያሰላሰልን፣

                በሺ ቤት መቁጠሩን ሳንማርልዎ፣

                አቶ ተክለፃድቅ ምነው መሔድዎ?

      እንግሊዝ ፈረንሳይ ጣሊያኖች እረፉ፤ ሃሳብ አይግባችሁ፣

      አይመጣም እንግዲህ የኢትዮጵያን ታሪክ የሚጠይቃችሁ።

                                                  ያፄ ልብነ ድንግል የቦካን ተራራ፣

                                                  ያፄ ፋሲል ጎንደር የመቅደላ ጎራ፣

                                     እንደ ተክለፃዲቅ ከሌለህ ወዳጂ፣

                                     ማን ይፅፍልሃል ተረስተህ ቅር እንጂ።

                                                      ተክለፃዲቅ መኩሪያ የበቀለብሺ፣

                                                      ኩሪ አገሬ ቡልጋ ደብረ ፅላልሺ።

                                የተፈለፈለ የተሰራ ከአለት፣

                                እንደ ላሊበላ እንደ አክሱም ሐውልት፣

                                                  የታሪክ አምድ ነው ተክለፃዲቅ መኩሪያ፣

                                                 መናኸሪያ እሚሆን መነሻ መድረሻ።

                                                ታሪክ ይመላለስ እንደ ለመደው፣

                                                የማይመለሰው ተክለፃዲቅ ነው።

                                   ከዚያ ከትልቁ ከሰማይ ቤት፣

                                   የምትፅፈውን ታሪክ ለመስማት፣

                                  ልሂድ ካንተ ጋራ አብሬ ልሙት፣

                                ተክለፃዲቅ መኩሪያ የታሪክ አባት።

                 የተክለፃዲቅ ነፍስ ምን ቸግሯት ቦታ፣

                 ቢሻት ከአብርሃም ጎን ከነ ይስሃቅ ተርታ፣

                 ቢሻት ከቴዎድሮስ ከዮሐንስ ጋራ፣

                ቢሻት ከምንልክ ከተፈሪ ጋራ፣

               ትኖራለች የትም እንደ ልቧ ሆና፣

               እየፃፈች ታሪክ በጽድቅ ብራና።

                           ታሪክ አልማርም ባፍንጫዬ ይውጣ፣

                           ተክለፃድቅ መኩሪያ መምሕሬ ከታጣ።

                                                          ጥያቄ አትጠይቁኝ አታስቸግሩኝ፣

                                                          ተክለፃድቅ መኩሪያ ማነው አትበሉኝ፣

                                                          ጣይ ሞቆት ጣይ ሞቆት አገር ያወቀው፣

                                                         ተረት ተረት ሳይሆን ታሪክ ፃፊ ነው።

ተክለ ፃድቅ መኩሪያ

የታላቁን ሰው የህይወት ታሪክ የማያውቅ አይኖርም ቢሆንም አብዘሀኛ ደራሴዎችም ሆኑ እንደራሴወች የጥብብ ሰዎችም ይህን ታላቅ ደራሲ ሲያነሱት አልያም ሲያወሱት አይታይም። እንደዚህ አይንት የጥበብ ሰወችን ለትውልድ አይን እና ጆሮ የሆነን ትላንትን በዛሬ ታሪክን ለባለታሪኩ ያሰረከቡንን የታሪክ አባቶችን ማሰታወሰ  ተገቢ ነው። በ1992 በላዕከ ተክለማርያም  ለዚህ እንቁ ሰው ለተክለፃዲቅ መኩሪያ መታሰቢያ የተገጠመች ስንኝ ብቻ አቀረብኩላችሁ።

የተክለፃድቅን ስራዎች ዋጋ የምንሰጣቸው በሚከተሉት ምክንያቶች ነው፦
➥ ታሪክን ከተተበተበበት ልማዳዊ አጻጻፍ ነፃ አውጥተው በሳይንሳዊ መንገድ መፃፍ በመጀመራቸው
➥ ሀገራዊውን መረጃም ሳይተው በፈረሳይኛ ፣ ጣልያንኛ እና እንግሊዝኛ ሁሉ ያለውን ተጠቅመው ከስር እስከ ጫፍ የሃገሪቱን ታሪክ በመፃፋቸው
➥ እነኚህን ሁሉ መጽሐፍት የፃፉት በመደበኛ የቀለም ትምህርት ሳይሰለጥኑ በከፍተኛ የመንግሥት ስራና ሃላፊነት ተጠምደው ያላቸውን የመዝናኛ ግዜ ሁሉ ሰውተው ቁምነገር በመስራታቸው
➥ በተለይ ከ15 አመታት በላይ የደከሙበት የግራኝ አህመድ ወረራ የተሰኘ መጽሐፋቸው በ155 ምእራፎችና በ840 ገፆች በጽሑፍ በካርታ በሰንጠረዥ በፎቶግራፍ መረጃዎች ተሞልቶ ስርአት ባለው መልኩ ታሪኩ ትንትን ተደርጎ የተሰራ በመሆኑ

ተክለፃድቅ መኩሪያ  የሃገሩን ሰርዶ በሃገሩ በሬ ያስወቁ ድንቅ የታሪክ ፀሐፊ ናቸው። አስባችሁታል ግን? ተክለፃድቅ መኩሪያ ባይኖሩ ኖሮ የኢትዮጵያን ታሪክ የምናነበው በጣልያንኛ ነበር። እጣ ፈንታ ተክለፃድቅ መኩሪያን ለዚህ ታላቅ ተልእኮ አጭታቸው ነበር፤እሳቸውም ትከሻቸውን አደንድነው ተልእኮውን ተቀብለው በሚገባ አሳክተዋል።

ምንጭ፦ ጆን አጋፔ (book for all page) 

አዘጋጅ፦ የታሪክ ክፍል 


የአማራ ትስስር በቻይና

መስከረም  3  2015 ዓ.ም 

ቻይና


የአማራ ትስስር በቻይና(ANiC)

የአማራ ሕዝብ የሚያኮራ ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ስነጽሑፍ፣ ሃይማኖትና ባህል ያለው፤ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ቅርሶች ባለቤት የሆነ፤ ሃገር የሰራ፣ ነጻነቱን ያስጠበቀ፤ የራሱ የሆነ ፊደል ያለው፤ የጥንታዊ ትምህርት ስርዓት ባለቤት የሆነ ጀግናና ኩሩ ሕዝብ ነው። የአማራ ሕዝብ በሃገረ መንግስት ምስረታ ሃገርን ከወራሪ መጠበቅና ዳር ድንበሯን በማስጠበቅ ታላቅ ገድል በመስራት እኛ ልጆቹ ቀና ብለን እንድንሄድ አድርጎናል።

Post a Comment

ቀዳሚ ገጽ ተከታይ ገጽ
hi