ይህ የአማራ ትሥሥርር በቻይና ይፋዊ ድረ-ገጽ ነው። በዚህ ድረ-ገጽ የአማራን ሕዝብ ታሪክ፣ ሃይማኖት፣ ባሕል፣ ልማድ፣ አርበኝነት፣ ቅርስ እና ሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮችንም ጭምር ለአባላት በሚገባ እናሳውቃለን። የድረ-ገጹ ዋና አላማ የአማራን ታሪክ በሚገባ ለሁሉም በማስተማር ታሪካችንን ወደቀደመ ልዕልናው መመለስ ነው። አንድ አማራ ለሁሉም አማራ፤ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ፤ አንዲት ነጻ ሃገር ኢትዮጵያ -->

Tesfa G/Selassie

የልሂቃን የጥበበኞች እና የጀግኖች ሀገር ሸዋ

የፊደል ገበታው ጌታ ቀኝ አዝማች ተስፋ ገብረ ሥላሴ ዘብሄረ-ቡልጋ

ከእፅዋት ቀለም አንጥረው፣ ከሸምበቆ ብዕር ቀርፀው፣ የፍየል ቆዳ ፍቀውና አለስልሰው በመጻፍ ሀ..ሁ… ዕውቀት ይስፋ፣ ድንቁርና ይጥፋ ይህ ነው የኢትዮጵያ ተስፋ የሚል መፈክር ተጠቅመው ወደ ማህበረሰቡ ያዘለቁት የፊደል ገበታው ጌታ ቀኝ አዝማች ተስፋ ገብረ ሥላሴ ዘብሄረ-ቡልጋ የተወለዱት ሰሜን ሸዋ፣ ቡልጋ ክታብ ወይራ አክርሚት ከተባለ ቀበሌ ነው።

ቀኝ አዝማች ተስፋ ከአባታቸው ከመምህር ገብረሥላሴ ቢልልኝ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ ሥዕለሚካኤል ወልደአብ ታህሳስ 24፣1895 ዓ.ም ተወለዱ። የፊደል ገበታ አባት የሚል ቅፅል መጠሪያ ያገኙት ተስፋ ገብረሥላሴን የሕይወትና የሥራ ታሪክ የሚያስቃኘው መፅሐፍ፤ ስለአማርኛ የፊደል ገበታ ፈጣሪዎች ማንነትና ዘመን ማብራሪያ ባይኖረውም፣ ባለታሪኩ በመጀመሪያ በብራና ላይ በእጃቸው እየፃፉ፣ በመቀጠልም በማተሚያ ቤት ማሽን እያባዙ ለህዝብ እንዲደርስ አድርገዋል።

ምስል :- ቀኝ አዝማች ተስፋ ገብረ ሥላሴ


የአማርኛ የፊደል ቅርፅ በወቅቱ በእንጦጦ ማርያም፣ በባዕታ ለማርያምና በመካነ ኢየሱስ ሥላሴ አጥቢያዎች እንዲሁም በገጠር አብያተ ክርስትያናት፤ በገዳማትና በዋሻዎች ብቻ ተወስኖ እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ። ይህ ፍንጭ አጥኚዎች የፊደል ገበታውን በእነዚህ ተቋማት ያኖረው ሰው ማነው ብለው እንዲጠይቁ የሚያግዝ ጥቆማ ነው። ተስፋ ገብረሥላሴ በ1909 ዓ.ም የ15 ዓመት ልጅ ሆነው ከትውልድ መንደራቸው ወደ አዲስ አበባ ሲመጡ ያረፉበት መንደር አራት ኪሎ ነበር። በዚያ ዘመን ከአራት ኪሎ የከተማዋ ደማቅ አካባቢ፤ አዝማሪ የማይታጣበት የቆንጆዎች መቀጣጠሪያ ነበር ይላል በመፅሃፉ ገፅ 29 የሰፈረው መረጃ። ተስፋ ገብረስላሴ አዲስ አበባ ከመጡ በኋላ ሰርተው ራሳቸውን ለመቻል በእንጨት ፈለጣ፣ ውሃ በመቅዳት፣ ጉድጓድ በመቆፈር፣ በጎዳና ንግድ እና መሰል ትናንሽ ስራዎች ላይ ተሳትፈዋል። ነጋድራስ አቡበከር ከጅቡቲ ከሚያስመጧቸው በተለይ ሽቶ እየተቀበሉ በየሆቴሉ ዞረው ሸጠዋል። በዘመኑ በአራት ኪሎ መንደር በንግድ ስራቸው በጣም ታዋቂ የነበሩት ነጋድራስ አቡበከር የአፋር ብሄረሰብ ተወላጅ ነበሩ። ከፈረንሳይ አገር የሚያስመጡትን ሸቀጥ በጅቡቲ በኩል ወደ አዲስ አበባ በማስገባት አገልግሎት ሲሰጡ በዕድሉ ከተጠቀሙት አንዱ ነበሩ።

ክስ፣ እስርና ውንጀላ ያልተለያቸው ባለታሪክ የተስፋ ገብረሥላሴን የስራና የህይወት ታሪክን ማዕከል አድርጎ የአገራችንን ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ ጉዳዮች በስፋት የሚያስስ ዘመን ተሻጋሪ ባለ-ውለታ መፅሐፍ፤ ባለ ታሪኩ የህዝብና የአገር ባለውለታ መሆን የቻሉት በብዙ ውጣ ውረድ ውስጥ አልፈው እንደሆነ ይገልፃል። በንጉሡ ዘመን (ከኢጣሊያ ወረራ በፊትና በኋላ) ፣በጠላት ወረራ ወቅት፣ በደርግም አገዛዝ ለክስ፣ ለእስርና ውንጀላ ተዳርገዋል፡፡ በመጨረሻ ሁሉንም አሸንፈው በተደጋጋሚ ተሸላሚ ሆነዋል።

ከአፄ ኃይለሥላሴ መንግሥት የቀኝ አዝማች ማዕረግ ተሰጥቷቸዋል። የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር ደጋግሞ አመስግኗቸዋል። ታላቅ ተግባርና ትልቅ ስም አርቆ መድረሻን ለማቀድ፣ ከብዙ ጥረትና ልፋት የሚገኝ ነው። በዓመታት ድካም የተገነባ መልካም ተግባርና ስም ሊጠፋ፣ ሊረሳና ሊዘነጋ የሚችልባቸው ብዙ ምክንያቶች አሉ። እኔ ከሞትኩ በኋላ ጥረትና ድካሜ ምን ይሆናል ብሎ ቀድሞ አለማሰብ ታላቅ ተግባርና ስም እንዲጠፋ ሰበብ ከሚሆኑት አንዱ ነው።ቤተሰቦቻቸውን ባለ አክሲዮን በማድረግ ኃ.የተ.የግ.አ/ማህበር በ1991ዓ.ም ያቋቋሙት ባለታሪኩ፤ ሥራና መልካም ተግባራቸው እንዳይጠፋ ማድረግ ችለዋል።

ተስፋ ገብረሥላሴ ግንቦት 26 ቀን 1992 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ሲለዩ፣ የ97 ዓመት የዕድሜ ባለፀጋ ነበሩ።

ምንጭ፦ ከመታገስ ዋሌ ( ቆራጡ አማራ ገጥ ላይ የተወሰደ )

ቪዲዮ፦ ስለ ተስፋ ገብረ ሥላሴ ዘብሄረ ቡልጋ በትንሹ

የአማራ ትስስር በቻይና

ሐምሌ 28 ቀን 2014 ዓ.ም

ቻይና

የአማራ ትስስር በቻይና(ANiC)

የአማራ ሕዝብ የሚያኮራ ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ስነጽሑፍ፣ ሃይማኖትና ባህል ያለው፤ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ቅርሶች ባለቤት የሆነ፤ ሃገር የሰራ፣ ነጻነቱን ያስጠበቀ፤ የራሱ የሆነ ፊደል ያለው፤ የጥንታዊ ትምህርት ስርዓት ባለቤት የሆነ ጀግናና ኩሩ ሕዝብ ነው። የአማራ ሕዝብ በሃገረ መንግስት ምስረታ ሃገርን ከወራሪ መጠበቅና ዳር ድንበሯን በማስጠበቅ ታላቅ ገድል በመስራት እኛ ልጆቹ ቀና ብለን እንድንሄድ አድርጎናል።

Post a Comment

ቀዳሚ ገጽ ተከታይ ገጽ
hi