ይህ የአማራ ትሥሥርር በቻይና ይፋዊ ድረ-ገጽ ነው። በዚህ ድረ-ገጽ የአማራን ሕዝብ ታሪክ፣ ሃይማኖት፣ ባሕል፣ ልማድ፣ አርበኝነት፣ ቅርስ እና ሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮችንም ጭምር ለአባላት በሚገባ እናሳውቃለን። የድረ-ገጹ ዋና አላማ የአማራን ታሪክ በሚገባ ለሁሉም በማስተማር ታሪካችንን ወደቀደመ ልዕልናው መመለስ ነው። አንድ አማራ ለሁሉም አማራ፤ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ፤ አንዲት ነጻ ሃገር ኢትዮጵያ -->

Ashenda festival in St. Lalibela(የአሸንድዬ በዓል በላስታ ቅዱስ ላሊበላ)

 💫የአሸንድዬ በዓል በላስታ ቅዱስ ላሊበላ💫

የአሸንድዬ በዓል በነሐሴ ወር አጋማሽ የጾመ ፍልሰታ ለማርያምን ፍጻሜ ተከትሎና የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በዐለ ዕርገት መሠረት አድርጎ የሚከበር ነው። ፍልሰታ የሚለው ቃል የድንግል ማርያምን ሥጋ ከጌቴሰማኒ ወደ ገነት መፍለሱን፤ ኋላም በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር ከነበረበት መነሣቱን ለማመልከት የሚነገር ቃል ነው። መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረቱ በመዝሙረ ዳዊት ምዕራፍ ፻፴፩ ፥  ላይ  ተነሥዕ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ አንተ ወታቦተ መቅደስከ (አቤቱ ወደ ዕረፍትኽ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስኽ ታቦት)  የሚለው ነው። ጾመ ፍልሰታ በፍትሐ ነገሥት በአንቀጽ ፲፭ ከተዘረዘሩት ሰባቱ አጽዋማት አንዱ ሁኖ ከነሐሴ ፲፭ የሚጾም ነው። 


የባሕላዊው ጫዎታው ስያሜ የተወሰደው ልጃገረዶች ጠላልፈው በመጎንጎን በጀርባቸው አሥረው ከሚወዘውዙት አሸንዳ ተብሎ ከሚታወቅ ቀጤማ መሰል ሣር ነው። ይህ በላስታ አሸንድዬ ተብሎ የሚታወቀው የልጃገረዶች ባሕላዊ ጨወታ በዋግ ሻደይበራያ ቆቦ ሶለል በመባል ተቀራራቢነት ባላቸው ስያሜዎች ይጠራል። በሁሉም አካባቢዎች የሚታየው የአከባበር ሁኔታና ቀኑም ተመሳሳይ ነው። አብዘሀኛውን ጊዜ የአሸንድዬ ባሕላዊ ጨዋታ የሚከናወነው ከነሐሴ ፲፮-፳፩ ባሉት አምስት ቀናት ነው።  

ለአሸንድየ በዓል መከበር መነሻ ምክንያት ናቸው የሚባሉ የቀደሙ የመጽሐፍ ቅዱስ አበው ታሪክ አልፎ አልፎም ቢሆን ይጠቀሳል። ከእነዚህም መካከል ከእሥራኤል መሳፍንት መካከል የዮፍታሔ ልጅ መታሰቢያ ልጆች ወይም ደናግል በየዓመቱ ሲያከብሩት የነበረውን በዓል እንደ አብነት በመውሰድ ነው የሚሉ አሉ።  ሌሎች ደግሞ የአሸንዳን በዓል ከሊቀ ነቢያት ሙሴ መወለድ እና ውሃ ዳር ከቀጤማ ሥር መጣል ጋራ ያያይዙታል። በግብጽ አገር ሙሴ እንደተወለደ ማንኛውም ወንድ ዕብራዊ ሲወለድ እንዲገደል በግብጽ ዐዋጅ መውጣቱን ተከትሎ እናቱ እግዚአብሔር እንዳደረገ ያድርገው ብላ ከዐባይ ወንዝ ዳርቻ በቄጤማ ውስጥ አስቀምጣዋለች። በኋላ ግን የፈርዖን ልጅ ገላዋን ልትታጠብ ወደ ወንዝ (ዐባይ) ስትሄድ ደንገጡሯን ልካ አውጥታ በእናቱ ሞግዚትነት አሳድጋው እሥራኤልን ከተገዙበት የአራት መቶ ሠላሳ ዓመት ባርነት ነጻ እንዳወጣቸው ይታወቃል። ከዚህም በመነሳት ሙሴ የተጣለበትን ቄጤማ ስያሜ ወስዶ አሸንድዬ ተባለ ይላሉ። ልጃገረዶቹ በጨዋታቸው አበ ሙሴ፣ ወርቃ በሙሴ እያሉ ደጋግመው ማንሣታቸውን ለዚህ ማስረጃ አድርገው ያቀርባሉ።

እነዚህና መሰል ጉዳዮች የአሸንድዬ ባሕላዊ ጨወታ መነሻ ተደርገው ቢወሰዱም ዋናውና በብዙዎች ዘንድ ተቀባይነት ያለው በዐል ግን ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ፍልሰት ጋራ እየተያያዘ የመጣው የአከባበር ሥነ ሥርዓት ነው። በጒንጒን ታሥሮና ተጠላልፎ ለጨዋታ የሚታሠረው የአሸንድዬ ቅጠል መላእክት እመቤታችንን ክንፍ ለክንፍ ገጥመው ተያይዘው የማሳረጋቸው ምሳሌ ተደርጎ ይወሰዳል። ልጃገረዶቹ አሸንድዬ የሚባለውን የሣር ዐይነት ቅጠል በወገባቸው ጠምጥመው ተያይዘው ሲዘፍኑ መላእክት ድንግል ማርያምን ክንፍ ለክንፍ ገጥመው እያመሰገኑ ማሳረጋቸውን ያመለክታል። 

ከዚህም ሌላ ሐመልማል ሙሴ በሲና ተራራ ከእሳት ጋር ተዋሕዶ ያየውን በቤተ ክርስቲያናችን በድንግል ማርያም የሚመሰለውን ቅጠል ይመሰላል ይላሉ። ሌሎች ደግሞ የአሸንድዬ ቅጠል ሔዋን ዕፀ በለስን በልታ ራቁቷን በኾነች ጊዜ ያገለደመችውን ቅጠል ሲያስታውስ አረንጓዴ መኾኑ ደግሞ በሥዕለ ማርያም ላይ የምንመለከተውን የድንግል ማርያምን ሐምራዊ የልብስ ቀለም ያስታውሳል ይላሉ። ከዚህ በተጨማሪ ልምላሜው የዐዲሱን ዓመት መምጣት ማብሰሪያም ተደርጎ ይወሰዳል። 

          የአሸንድዬ በዓል አከባበር በፎቶ


በዚህም ተባለ በዚያ የአሸንድዬ ባሕላዊ ጨዋታ መሠረቱም ሆነ አጠቃላይ እሳቤው ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጋር በተገናኘ ሃይማኖታዊ መሆኑን እንገነዘባለን። በመሆኑም ይህ በዓል መንፈሳዊ ይዘቱን ጠብቆ በቅዱስ ላሊበላ ከተማ በልዩ ልዩ ዝግጅቶች በድምቀት ይከበራል። በነሐሴ ፲፮ ቀን በሚከበረው ሁሉን አቀፍ የአደባባይ የአሸንድዬ ክብረ በዓል የቅዱስ ላሊበላ ደብር አሥተዳደር ካህናት ያሬዳዊ ዝማሬና ቅኔ ያቀርባሉ። 

በዚህ ቀን የደብረ ሮሓ ልጃገረዶች በየአጥቢያቸው በቡድን ይሰባሰቡና መጀመሪያ የሚሄዱት ወደ ቤተ ክርስቲያን ነው። ወደሌላው የበዓል ሥነ ሥርዓታቸው ከመሄዳቸው በፊት ቤተ ክርስቲያኑን ሦስት ጊዜ እየዘመሩ በመዞር እዚህ ላደረሳቸው አምላክ ምስጋና ያቀርባሉ። 

ከቤተ ክርስቲያን መልስም  ከታዋቂዎቹና ከሽማግሌዎቹ ጀምረው በየሰው ቤት እየሄዱ የደስታ መግለጫቸውን ያሰማሉ፤ የተለመደውን ባሕላዊ ጫወታቸውን ወይም ዘፈናቸውን ያቀርባሉ። ከዚያም ምርቃት ይደረግላቸዋል፤ ስጦታ ይሰጣቸዋል። በጫወታቸው ወቅት በዜማ እየተቀባበሉ የሚያቀርቧቸው ግጥሞችም መንፈሳዊ ይዘትና ትርጉም ያላቸው ናቸው። ልጃገረዶቹ ለበዓሉ የሚሆናቸው ልዩ ቀሚስና የሚዋቡበትም ልዩ ጌጣጌጥ አላቸው።

ምንጭ፦ ቅዱስ ላሊበላ ከሚለው የቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜ መጽሐፍ የተወሰደ

💧💧💧መልካም የአሸንድዬ በዓል💧💧💧

አዘጋጅየባሕል ክፍል

የአማራ ትስስር በቻይና
ነሐሴ 16 ቀን 2014 ዓ.ም
ቻይና


የአማራ ትስስር በቻይና(ANiC)

የአማራ ሕዝብ የሚያኮራ ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ስነጽሑፍ፣ ሃይማኖትና ባህል ያለው፤ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ቅርሶች ባለቤት የሆነ፤ ሃገር የሰራ፣ ነጻነቱን ያስጠበቀ፤ የራሱ የሆነ ፊደል ያለው፤ የጥንታዊ ትምህርት ስርዓት ባለቤት የሆነ ጀግናና ኩሩ ሕዝብ ነው። የአማራ ሕዝብ በሃገረ መንግስት ምስረታ ሃገርን ከወራሪ መጠበቅና ዳር ድንበሯን በማስጠበቅ ታላቅ ገድል በመስራት እኛ ልጆቹ ቀና ብለን እንድንሄድ አድርጎናል።

Post a Comment

ቀዳሚ ገጽ ተከታይ ገጽ
hi